Ethsat.com: በሰሜን ጎንደር ውጊያው ቀጥሎአል በርካታ ቤቶችም ተቃጥለዋል

From: Berhane Habtemariam <Berhane.Habtemariam59_at_gmx.de_at_dehai.org>
Date: Tue, 6 Dec 2016 23:56:07 +0100
በሰሜን ጎንደር ውጊያው ቀጥሎአል በርካታ ቤቶችም ተቃጥለዋል

Dec. 06, 2016

Watch this.

 

 

 
 

ኅዳር ፳፯ (ሃያ ሰባት)ቀን ፳፻ / ኢሳት ዜና :- በሰሜን ጎንደር በነጻነት ሃይሎች እና በአገዛዙ ወታደሮች መካከል የሚካሄደው ውጊያ እንደቀጠለ ሲሆን፣ ያልጠበቀው ጉዳት የደረሰበት አገዛዙ የአርሶአደሮችን ቤቶችን በማቃጠል የበቀል እርምጃ እየወሰደ ነው።

በወገራ ወረዳ በእንቃሽ ከትናንት በስቲያ ከ10 በላይ ቤቶች የተቃጠሉ ሲሆን፣ ዛሬ ማክሰኞ ደግሞ በጃኖራ አቶ መስፍን የተባሉ ታጋይ ሁለት ቤቶቻቸው የተቃጠሉባቸው ሲሆን፣ ከጠዋት እስካሁን የተኩስ ለውውጥ እየተካሄደ ነው።

ባለፉት ሳምንታት በተደረገው ውጊያ ከፍተኛ ጉዳት የደረሰው ጉዳት በመከላከያ ላይ መሆኑን የሚገልጹት የአካባቢው ምንጮች፣ በርካታ ቁጥር ያላቸው ወታደሮች አስከሬን ዛሬ መቀበሩን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

በሌላ በኩል በቋራ ወረዳ በርካታ ዜጎች መሳሪያ አስረክቡ እየተባሉ እየተደበደቡና እየታሰሩ ነው ።

በሰሜን ጎንደር  ዞን በ ቋራ ወረዳ በሊገበር ቀበሌ የሚገኙ በርካታ አርሶአደሮች በአካባቢው በተሰማሩት ታጣቂዎች ክፉኛ መደብደባቸውን ፣ አንዳንዶች ደግሞ ወደ ጫካ መግባታቸውን ነዋሪዎች ገልጸዋል። ድብደባውንና እስራቱን ለማምለጥ ጫካ የገቡ አርሶአደሮች ሚስቶች በቁጥጥር ስር ከዋሉ በሁዋላ፣ በታጣቂዎች ተገደው መደፈራቸውንም የአካባቢው ነዋሪዎች በምሬት ይገልጻሉ።

ዋና ሃይሌ እና ደረበ ደማስ የተባሉት አርሶአደሮች በድብደባ ብዛት እጃቸው ከጥቅም ውጭ መሆኑን የገለጹት ነዋሪዎች፣ ሌላ አርሶአደር ሽፍታ አብልታችሁዋል በመባላቸው ባልና ሚስቱ ታስረው፣ አምስት ልጆቻቸው ለችግር ተደርገዋል። አገዛዙ ራሱ ያስታጠቃቸውን ሚሊሺያዎች ሳይቀር መሳሪያቸውን መግፈፍ መጀመሩን ነዋሪዎች ይናገራሉ። ህብረተሰቡ ለታጣቂዎች በግዳጅ ምግብ እንዲያቀርብ እየተደረገ መሆኑንም ነዋሪዎች ገልጸዋል።

መሳሪያ የማስፈታቱ እንቅስቃሴ በሌሎችም የክልሉ ዞኖች እየተካሄደ ሲሆን፣ የጦር መሳሪያ እንደሌላቸው የገለጹ አርሶአደሮች እስር ቤቶችን እያጨናነቁ ነው።

በሰሜን ጎንደር በአገዛዙ ወታደሮችና በነጻነት ሃይሎች መካከል የሚደረገው ውጊያ እየጨመረ መምጣቱን ተከትሎ አገዛዙ መሳሪያ የማስፈታቱን እንቅስቃሴ አጠንክሮ እንዲገፋበት አድርጎታል።

*******************************************************************************
የኢትዮጵያ ገቢ ንግድ ከወጪ ንግድ ገቢ ያለው ልዩነት እየጨመረ መምጣቱ የአለም ባንክ አስታወቀ

Dec. 06, 2016

ኢሳት (ኅዳር 27 ፥ 2009)

የአለም ባንክ የኢትዮጵያ ገቢ ንግድ ከወጪ ንግድ ገቢ ያለው ልዩነት እየጨመረ መምጣቱንና ከ10 በመቶ በላይ መድረሱን ማክሰኞ ይፋ አደረገ።

በሃገሪቱ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ዙሪያ አምስተኛ ሪፖርትን ያወጣው ባንኩ የኢትዮጵያ የገቢና ወጪ ንግድ አለመመጣጠን በኢኮኖሚ እድገቱ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ  ማሳደሩን ገልጿል።

የኢትዮጵያ የስራ አጥ ችግርም ከአፍሪካ ሃገራት ጋር ሲነጻጸት በመጠን ከፍተኛ መሆኑን የባንኩ ሪፖርት አመልክቷል።

ባለፉት ጥቂት አመታት መታየት የጀመረው የኢትዮጵያ የውጭ ንግድ ገቢ መቀነስ በኢኮኖሚ ዕድገቱ ላይ ተፅዕኖ እያሳደረ መሆኑን ያስታወቀው የአለም ባንክ ሃገሪቱ በከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ችግር ውስጥ መሆኗንም አስታውቋል።

በኢትዮጵያ የተከሰተው የድርቅ አድጋ በኦሮሚያ ክልል ለአንድ አመት ያህል ጊዜ ሲካሄድ የቆየው ህዝባዊ ተቃውሞ በሃገሪቱ አጠቃላይ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩንም የባንኩ ሪፖርት ይገልጻል።

ሃገሪቱ አሁን አጋጥሟት ያለውን ሁለገብ ኢኮኖሚያዊ ችግር ለመፍታት የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ከማሳደግ በተጨማሪ የስራ አጥነት ችግርን መቅረፍ እንዲሁም የኢኮኖሚ ፖሊሲ ማሻሻያዎችን ተግባራዊ ማድረግ እንደሚያስፈልግ የአለም ባንክ የመፍትሄ ሃሳብ ብሎ ለመንግስት ካቀረባቸው ነጥቦች መካከል ዋነኞቹ ናቸው።

መንግስት የ2015/2016 አም የኢክኖሚ ዕድገቱ በሁለት አህዝ ያድጋል ብሎ የነበረ ቢሆንም የአለም ባንክ ዕድገቱ በስምንት በመቶ አካባቢ መመዝገቡን አክሎ አስፍሯል።

በኢትዮጵያ ያለው የስራ አጥነት ችግር በኢኮኖሚ ዕድገቱ ሊፈታ አለመቻሉን ያወሳው ባንኩ ከ20 በመቶ በላይ ላይ የሚገኘው የስራ አጥ አህዝ ከአፍሪካ ሃገራት ጋር ሲነጻጸር ከፍተኛ መሆኑን ይፋ አድርጓል።

ሩዋንዳ፣ ዩጋንዳና ሌሎች የአህጉሪቱ ሃገራት የስራ አጥ ቁጥራቸው ከ10 በመቶ በታች ሲሆን፣ ኢትዮጵያ በዘፍሩ ያለባትን ችግር ለመፍታት የተለያዩ ዕርምጃዎችን መውሰድ እንደሚገባት ባንኩ አክሎ አሳስቧል።

የአለም ባንክና ሌሎች የፋይናንስት ተቋማት ከ36 ቢሊዮን ዶላር በላይ የደረሰው የሃገሪቱ የእዳ ክምችት ኢኮኖሚያዊ ዕድገቱን ሲፈታተን መቆየቱን ሲገልጹ ቆይተዋል።

በውጭ ብድር በመካሄድ ላይ ያሉ የልማት ፕሮጄክቶች በታቀደው መሰረት ተግባራዊ ሊሆኑ ካልቻሉ በቀጣዩ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ ተጨማሪ ተፅዕኖን ሊያሳድሩ ይችላሉ ሲሉ በባንኩ የአፍሪካ የማክሮ ኢኮኖሚ ባለሙያ የሆኑት ፓሎማ ካሴሮ ገልጸዋል።

Received on Tue Dec 06 2016 - 17:56:06 EST

Dehai Admin
© Copyright DEHAI-Eritrea OnLine, 1993-2013
All rights reserved