Basic

Goolgule.com: በጎንደር ከተማ በተቀሰቀሰው ህዝባዊ አመጽ ንብረታቸዉ ወድሟል የተባሉ የትግራይ ሰዎች ካሳ ሊከፈላቸዉ ነዉ

Posted by: Berhane Habtemariam

Date: Monday, 13 February 2017

በጎንደር ከተማ በተቀሰቀሰው ህዝባዊ አመጽ ንብረታቸዉ ወድሟል የተባሉ የትግራይ ሰዎች ካሳ ሊከፈላቸዉ ነዉ

 

በ2008ዓ.ም. መገባደጃ ወራት ላይ የወልቃይት የአማራ ማንነት ጥያቄ አስተባባሪ የኮሚቴ አባላትን የህወሃት/ኢህአዴግ ኃይሎች በጎንደር ከተማ ለማፈን ያደረጉት ሙከራ ከፍተኛ ህዝባዊ ቁጣ ቀስቅሶ የህይወትና የንብረት ዉድመት መድረሱ ይታወሳል። በወቅቱ “ንብረታቸው ወድሟል” የተባለላቸው የትግራይ ተወላጆች የካሣ ክፍ ሊፈጸምላቸው መሆኑ ለጎልጉል የደረሰው መረጃ ያመለክታል።

በጎንደር ከተማ በተቀሰቀሰዉ ህዝባዊ ተቃዉሞ “የትግረኛ ቋንቋ ተናጋሪዎች ንብረት እየተለየ ጥቃት ደርሶበታል” በሚል በህወሃት/ኢህአዴግ (“የፌዴራል መንግሥት”) የበላይ አደራጅነት በኢትዮጵያ ልማት ባንክ በኩል ጎንደር ከተማ ለሚኖሩ ትግራዋያን ነጋዴዎች “የጠፋባቸዉንና የወደመባቸዉን ንብረት” ለኢትዮጵያ ልማት ባንክ በማስመዝገብ የካሳ ክፍያና እንደ አስፈላጊነቱ የረዥም ጊዜ የብድር አገልግሎት ሊመቻችላቸዉ እንደሆነ የጎልጉል ታማኝ የመረጃ ምንጮች ከጎንደር ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽ/ቤት ያገኘነዉ መረጃ ያመለክታል።

ከኢትዮጵያ ልማት ባንክ ተወክለዉ የተላኩ ከፍተኛ ባለስልጣናትና የንብረት ገማች ባለሙያዎች ጎንደር ከተማ ተገኝተዉ “ተአረፉና ወደሙ” የተባሉ የትግራዋያንን የንግድ ደርጅቶች ወርቅ ቤቶችን፣ ሱቆችን፣ ሆቴሎችንና መኖሪያ ቤቶችን ተዘዋዉረዉ ጎብኝተዋል። እንደ ጎልጉል የመረጃ ምንጮች  በጎንደር ከተማ በንግድ ሥራ የተሰማሩ ትግራዋያኖች ከፍተኛ ግነት ባለዉ መልኩ ያልጠፋቸዉን ንብረቶች (በስቶክ ያልተመዘገቡ) አስመዝግበዋል።በተለይም የሁመራ፣ የተክሌ፣ የመሀሪ ወርቅ ቤት ባለቤቶች በህዛባዊ ተቃዉሞ ጊዜ ወርቅ ቤቶቻቸዉ ተዘግተዉ የነበረ በመሆኑ በርና መስኮታቸዉ ላይ በድንጋይ ድብደባ ጉዳት ከመድረሱ ዉጪ ይህ ነዉ የሚባል ንብረት ባልተዘረፈበት ሁኔታ ከፍተኛ የንብረት ዉድመት መድረሱንና በሚሊዮኖች ብር የሚያወጣ ወርቅ መዘረፋቸዉን አስመዝግበዋል።

ቅዳሜ ገበያ በተቃጠለበት ጊዜ

በተመሳሳይ መልኩ የሁመራ ፔንሲዮን፣ ጣና ሆቴል፣ ሮማን ሆቴልና ቋራ ሆቴል ባለቤት የሆኑ ትግራዋያን ወደመብን የሚሉትን ንብረት በሚሊዮኖች ደረጃ አስመዝግበዋል። በአንጻሩ በጎንደር ከተማ የሚኖሩ አማሮች በህዝባዊ ተቃዉሞዉ ጊዜ የወደመባቸዉ ንብረት በከተማ አስተዳደሩ እንዲመዘገብላቸዉ በተደጋጋሚ ቢያመለክቱም “ከክልል ትዕዛዝ አልተሰጠንም” የሚል ምላሽ ሲሰጣቸዉ ቆይቷል። በተለይም ከትግራይ ክልል በመጡ ሰርጎ ገቦች እንደተፈጸመ የሚጠረጠረዉ የከተማዋ ዋና የገበያ ማዕከል የሆነዉ “ቅዳሜ ገበያ” 446 የባህልና የዘመናዊ አልባሳት መሸጫ ሱቆች፣የጫማና ልዩ ልዩ ሸቀጣሸቀጦችና መደብሮች “በድንገተኛ” የእሳት አደጋ ሙሉ በሙሉ የወደመባቸዉ ነጋዴዎች ዛሬም ድረስ አስታዋሽ አጥተዉ ባሉበት ሠዓት ለትግራዋያን ተወላጆች ብቻ ለይቶ የካሳ ክፍያ ለመፈጸም ቅድመ ሁኔታዎች መጠናቀቃቸዉ የከተማዋን ተወላጆችና ተጎጅዎችን እንዳሳዘናቸዉ የጎልጉል የመረጃ ምንጮች ከወደ ጎንደር ያደረሱን መረጃ ያመለክታል።

“በርግጥ ኢትዮጵያ ዛሬም ያልተሟላች ሀገር ነች። ለአንዱ ማርና ወተት የምታዘንብ ለሌላዉ ደግሞ መዐትና መከራ የምታወርድ ጉራማይሌ ሀገር ሆናለች። ተስማማንበትም አልተስማማንበትም በአንድ ሀገር እየኖርን በዚህን ያህል መጠን መለያየታችን እጅግ አሳዛኝ ክስተት ነዉ። በአደባባይ አይን ያወጣ የብሄር መድሎ መፈጸም ሀገሪቱን ፍጹም ወደ አልተፈለገ መስመር ይመራታል እንጅ መፍትሄ አይሆንም። ትግራዋያንም ቢሆን በዚህን ያህል መጠን እንደ ብሄር ሊባል በሚችል መልኩ የሀገር ሀብት ቅርምት ተሳታፊ መሆናቸዉ ለነገ ዉርስ ዕዳ እያስቀመጡ መሆኑን ሊያዉቁት ይገባል። የሀገራችን ሰዉ “ግርግር ለሌባ ይመቻል!” እንደሚል የጎንደሩን ህዛባዊ ቁጣ ያስታከኩ ትግራዋያን ባለሀብቶች ጎንደር ላይ ያልታሰበ የትርፍ ሲሳይ ዘንቦላቸዋል” በማለት ጉዳዩን በቅርብ የሚከታተሉ አስተያየት ሰጪ ለጎልጉል ተናግረዋል።


EmbassyMedia - ራብዓይ ግንባር!

Dehai Events