Basic

Ethsat.com: ኦህዴድና ሶህዴፓ እርስ በርስ እየተወነጃጀሉ ነው

Posted by: Berhane Habtemariam

Date: Thursday, 14 September 2017

ኦህዴድና ሶህዴፓ እርስ በርስ እየተወነጃጀሉ ነው

(ኢሳት ዜና–መስከረም 4/2010)ኦህዴድና ሶህዴፓ እርስ በርስ እየተወነጃጀሉ ነው።

Watch.

ESAT Daily News Amsterdam September 14,2017

https://ethsat.com/2017/09/esat-daily-news-amsterdam-september-142017/

ESAT DC Daily News Thur 14 Sept 2017

በኦሮሚያና በኢትዮጵያ ሶማሌ አዋሳኝ አካባቢዎች ሰሞኑን ከተከሰተውና ተባብሶ ከቀጠለው እልቂት ጋር ተያይዞ የሁለቱ ክልላዊ መንግስታት ቃል አቀባይ ቢሮዎች አንዱ ሌላኛውን ተጠያቂ የሚያደርግበት መግለጫ አውጥተዋል።

በአቶ አብዲ መሀመድ ኦማር የሚመራው የሶማሌ ክልላዊ መንግስት ባወጣው መግለጫ ሰሞኑን በኦሮሚያና ሶማሌ ወሰን አካባቢ የተነሳው ግጭት በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት የሚደገፍና በክልሉ የታጠቁ ሃይሎች፣በክልሉ ፖሊስ፣ሚሊሺያና የኦነግ ቄሮ አባላት የተቀነባበረ እንደሆነ ገልጿል።

የኦሮሚያ ክልል ኮሚኒኬሽን ቢሮ ሃላፊ አቶ አዲሱ አረጋን ደግሞ በግልጽ የኦነግ አባልነቱን በተግባር ያረጋገጠ በማለት ከሶታል።

ሰሞኑን በአወዳይ ከተማ ከ50 በላይ ንጹሃን ዜጎች በአሰቃቂና እስከዛሬ በሀገራችን ታይቶ በማይታወቅ መልኩ ተገድለዋል ብሏል።

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት በክልሉ ነዋሪ በሆኑ የሶማሌ ተወላጆች ላይ የጀመረውን የዘረኝነት ጭፍጨፋ አጠናክሮ መቀጠሉን ያመላክታል በማለት በመግለጫው ዘርዝሯል።

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስትና የጸጥታ ሃይሉ በክልሉ ላይ ከ20 አመት በላይ የኖሩ ከክልሉ ማህበረሰብ ጋር በደም የተዛመዱ የሶማሌ ተወላጆች ላይ የወሰደው ርምጃ የሱማሌ ክልል ህዝብና መንግስትን በእጅጉ አስቆጥቷል ብሏል።
ጉዳት አድራሾቹ በህግ ተጠያቂ የሚሆኑበትን ሁኔታ ለመፍጠር አጥብቆ እንደሚሰራ አሳስቧል።

በአቶ ለማ መገርሳ የሚመራው የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ለአጸፋ ምላሽ ባወጣው መግለጫ የሶማሌ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ያወጣው መግለጫ እጅግ በጣም አሳፋሪና ሃላፊነት የጎደለው ነው ብሎታል።
የተጣለበትን ሕዝባዊና መንግስታዊ ሃልፊነት ከመሸሽም አንጻር ደካማ ቁመናና ዝቅተኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ በማለት ፈርጆታል።

መግለጫው የሶማሌ ክልላዊ መንግስት ልዩ ሃይል አደራጅቶ ሰላማዊ ዜጎች ላይ ጥቃት ማድረሱና ሰላማዊ ዜጎች ኦሮሞ በመሆናቸው ብቻ ቀያቸውን ጥለው እንዲሰደዱ መደረጉ ከፌደራሊዝሙ በተቃራኒ መቆሙን ያመላክታል ብሏል።

የሶማሌ ክልላዊ መንግስት የለማ መገርሳን አስተዳደር በአሸባሪነትና በኦነግነት ፈርጆ ያወጣው መግለጫ ሀላፊነት በጎደለው አግባብ የተጻፈና ወንጀልም ጭምር በመሆኑ ህገመንግስቱን ተከትለን በህጋዊና በአስተዳደራዊ መንገድ የምንጠይቅ መሆኑን እንገልጻለን በማለት ያስጠነቅቃል።

መግለጫው ከዚህ በፊት የኦሮሞ ተወላጆችንና የክልሉን አመራሮች በኦነግነት መፈረጅና ለማሸማቀቅ መሞከር ከበርካታ አመታት በፊት ሲደረግ የነበረ አሁን ጊዜው ያለፈበት ተራ ፍረጃ መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን በማለት ያስገነዝባል።
መግለጫው ከዚህ በፊት የኦሮሞ ተወላጆችን በኦነግነት የሚፈርጀው አካል ማን እንደሆነ የገለጸው ነገር የለም።

በፖለቲካ ተንታኞች ዘንድ ግጭቱን ከጀርባ ሆኖ በማቀነባበር የሚወቀሰው ይህወሃት ቡድንም ሆነ የፌደራል መንግስቱ ፍጅቱን ለማስቆም ዳተኛ ሆነው ተገኝተዋል።

*******************************************************************************

በኦሮሞና ሶማሌ ወሰኖች ላይ የተጀመረው ግጭት ተባብሶ መቀጠሉ ተገለጸ

(ኢሳት ዜና–መስከረም 4/2010) በኦሮሞና ሶማሌ ወሰኖች ላይ የተጀመረው ግጭት ተባብሶ መቀጠሉ ተገለጸ።

በሺዎች የሚቆጠሩ የኦሮሞ ተወላጆች ከሶማሌ ክልል የተለያዩ ከተሞች ተፈናቅለው ወደ ሀረር መግባታቸው ታውቋል። ሁለቱ ክልሎች እየተወዛገቡ ነው።
ከሁለቱም ወገኖች በርካታ ሰዎች ተገድለዋል። ግጭቱ ወደ አጠቃልይ ቀውስ ሊያመራ እንደሚችል እየተነገረ ነው።

የሃይማኖት አባቶች ጥሪ አስተላልፈዋል። ይህ ግጭት በአገዛዙና በህዝብ መካከል ብቻ መሆኑን በሶማሌ እና ኦሮሚያ አካባቢዎች የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በኢሳት በኩል መልዕክት እንዲደርስላቸው ጠይቀዋል።
የሁለቱ ክልሎች መንግስታት እየተወነጃጀሉ ነው። ሁለቱም ወገኖች በየፊናቸው የሚያሰራጯቸው መልዕክቶች ግጭቱን ከማብረድ ይልቅ እንዲባባስ ምክንያት መሆኑም እየተነገረ ነው።

ይሄን ያህል ዜጎች ሲገደሉና ከሚኖሩበት ተባረው ሲወጡ በዝምታ እየተመለከተ ያለው የህወሃት መንግስት ለ26 አመታት የተከተለው የዘር ፖለቲካ ውጤት ነው የሚለው ድምዳሜ በብዙ ወገኖች ዘንድ እየተሰጠ ነው።
ለኢሳት የሚደረሱ መረጃዎች አሰቃቂ በመሆናቸው ለህዝብ ደህንነት ሲባል እንዳይተላለፉ መደረጋቸው ተገልጿል።

ባለፉት ሶስት ቀናት ከሶማሌ ክልል የተለያዩ ከተሞች በተለይም ከጂጂጋና ውጫሌ በመታወቂያቸው በሰፈረ የብሄር ማንነት እየተለዩ የሚገደሉ፣ የሚታሰሩ የኦሮሞ ተወላጆች ቁጥር እየጨመረ መቷል።

ይህን በመስጋት ቤት ንብረታቸውን ትተው የተሰደዱ የኦሮሞ ተወላጆች ወደ አቅራቢያ የኦሮሚያ መንደሮች እየገቡ ሲሆን በሀረር ከተማ በሺዎች የሚቆጠሩ መድረሳቸውን ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

ለኢሳት ዛሬ በደረሰው መረጃ በሺ ዎች የሚቆጠሩ የኦሮሞ ተወላጆች ከጅጅጋ በመውጣት ላይ ናቸው።

እስከ 12 ሺ የሚሆኑት ከሶማሌ ክልል እንደሚፈናቀሉ አንድ ባለስልጣን ለዘጋቢያችን ገልጸዋል።

ተፈናቃዮቹ በሽሽት ላይ እያሉ በመንገድ ላይ ግጭት ተከስቷል ተብሏል። ስለደረሰው ጉዳት ግን ዝርዝር መረጃ እየጠበቅን ነው።

ጥቃቱን እየፈጸሙ ያሉት የሶማሌ ልዩ ሃይል አባላት መሆናቸውን ተፈናቃዮች ይናገራሉ።

በሶማሌ ተወላጆች በኩልም ግድያና መፈናቀል እንደደረሰባቸው የሚገለጹ መረጃዎች በመውጣት ላይ ናቸው።

የኦሮሚያ ክልል የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ባወጣው መግለጫ በሶማሌ ልዩ ሃይል የጭካኔ እርምጃ የተቆጡ የኦሮሞ ተወላጆች ባደረጉት የተቃውሞ ሰልፍ ላይ ግጭት ተፈጥሮ 18 ሰዎች መገደላቸውን አስታውቋል። ከእነዚህም ውስጥ 12ቱ የሶማሌ ተወላጆች መሆናቸው ተገልጿል።

ዛሬ በሃረር ተቃውሞ መካሄዱ ተሰምቷል። ሸዋ በር እና ፈረስ መጋላ አካባቢ የአጋዚ ወታደሮች አንድ ሰው መግደላቸው የተገለጸ ሲሆን ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ ውጥረት መንገሱን ነው መረጃዎች የሚያመለክቱት።
በድሬደዋም እንዲሁ ግጭት እንደነበረ የተገለጸ ሲሆን ስለደረሰው ጉዳት ግን የታወቀ ነገር የለም።

ሶማሌላንድ በተባለችው ሀገር የኦሮሞ ተወላጆች ላይ ጥቃት በመፈጸም ላይ መሆኑን ዘግይቶ የደረሰን መረጃ አመልክቷል። ለጊዜው ቁጥራቸው ያልታወቁ የኦሮሞ ተወላጆች በሶማሌላንድ መገደላቸውንም ከደረሰን መረጃ ለማወቅ ተችሏል።

በሌላ በኩል ለኢሳት በስልክ፣ በኢሜይና በፌስቡክ ከሀገር ቤት በተለይም በሶማሌና ኦሮሚያ ክልል ከሚገኙ ኢትዮጵያውያን በርካታ መልዕክቶች እየደረሱ ሲሆን ህዝቡ ከማንኛውም የእርስ በእርስ ግጭት ራሱን እንዲጠብቅና እንዲከላከል የሚጠይቁ ናቸው።

ይህ የህወሀት መንግስት ከህዝብ ጋር የገባበት ግጭት እንጂ በኢትዮጵያውያን መሀል የተፈጠረ አይደለም የሚለው መልዕክት በሁለቱም ክልሎች ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የተላለፉ ናቸው።


EmbassyMedia - ራብዓይ ግንባር!

Dehai Events