Basic

Satenaw.com: የአስቸኳይ ግዜ አዋጁ እና የህወሓቶች አሻጥር (የሰነድ ማስረጃ)

Posted by: Berhane Habtemariam

Date: Thursday, 22 February 2018

የአስቸኳይ ግዜ አዋጁ እና የህወሓቶች አሻጥር (የሰነድ ማስረጃ)

 

ስዩም ተሸመ

 

ጥቅምት 03/2010 ዓ.ም በተለያዩ የኦሮሚያ አከባቢዎች የተቃውሞ ሰልፍ ተካሂዶ ነበር። በወቅቱ “ይህን የተቃውሞ ሰልፍ ማን ነው የሚያስተባብረው?” የሚለው ጥያቄ ትልቅ መነጋገሪያ ሆኖ ነበር። በውጪ የሚገኙ የኦሮሞ ልሂቃን የተቃውሞ ሰልፉን እንዳልጠሩ ሲገልፁ ነበር። በተመሳሳይ አዲሱ የኦህዴድ አመራር በጉዳዩ ዘሪያ እጁ እንደሌለበት መግለፁ ይታወሳል። በእርግጥ ሰልፈኞች ከወትሮ በተለየ መልኩ የኦነግን ባንዲራ ይዘው ታይተዋል። በአንፃሩ የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ደግሞ ምንም ዓይነት አመፅና ሁከት እንዳይቀሰቀስ ጥብቅ ቁጥጥርና ክትትል ሲያደርግ ነበር። እኔ በግሌ ከታች የሚታየውን ፎቶ ሳነሳ ፖሊሶች ስልኬን ቀምተውኝ የነበረ ሲሆን ማንነቴን ከአጣሩ በኋላ ነው የመለሱልኝ።

ጥቅምት 03/2010 ዓ.ም በወሊሶ ከተማ የተካሄደው ሰላማዊ ተቃውሞ ሰልፍ (ethiothinkthank)

በሌላ እንደ ዳኒኤል ብርሃኔ ያሉ ቀንደኛ የህወሓት ደጋፊዎች “የተቃውሞ ሰልፉ እየተመራ ያለው ከተጠበቀው በላይ ትልቅ በሆነ የህቡዕ ድርጅት” መሆኑን ሲገልፁ ነበር። እኔም ጥቅምት 08/2010 ዓ.ም “የኦሮሞን መብት የበላ ኦነግ፥ ግብፅ፥ ዕቡዕ፥…እያለ ሲለፈልፍ ይውላል!” በሚል ርዕስ ባወጣሁት ፅሁፍ፤ “በኦሮሚያ ክልላዊ መስተዳደር ውስጥ በግልፅ ያልተለየ ‘ትልቅ የህቡዕ ድርጅት ተፈጥሯል’ በሚል ሰበብ በክልሉ ሕዝብ ላይ ሊፈፀም የሚችለው ግፍና በደል እንዳሳሰበኝ ገልጬ ነበር።

በእርግጥ ሰልፉ ላይ አንዳንድ የኦህዴድ አባላትና የደህንነት ሰራተኞች የኦነግ ባንዲራን ለሰልፈኞች ሲያድሉ እንደነበር በአካል ተመልክቼያለሁ። ይህ የተደረገበት መሰረታዊ ምክንያት ሰልፈኞች በአሸባሪነት የተፈረጀውን የኦነግ ባንዲራ በመያዝ ሁከትና ብጥብጥ እንዲያነሱ በማድረግ ሁኔታዎች ከቁጥጥር ውጪ እንዲወጡ ማድረግ ነበር። ሆኖም ግን፣ ፖሊሶች ከክልሉ መንግስት በተሰጣቸው ጥብቅ መመሪያ መሰረት ከሰልፈኞች ጋር በመነጋገርና በመግባባት በሰልፉ ላይ ምንም ዓይነት ሁከትና ብጥብጥ እንዳይፈጠር ማድረግ ቻሉ። በተለይ በወሊሶ ከተማ ጥቅምት 03/2010 ዓ.ም የተካሄደው ሰልፍ ፍፁም ሰላማዊና በሀገር ሽማግሌዎች ምርቃት ተጠናቀቀ። ይህን ማያያዣ በመጫን የቪዲዮ ምስሉን መመልከት ይችላሉ።

ሰላማዊ ሰልፉ ከተካሄደ ከአስር ቀናት በኋላ ጥቅምት 20/2010 ዓ.ም (በ28/10/2017) ከኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ከሚቴ አፈትልኮ የወጣ ሰነድ የተቃውሞ ሰልፉ አስተባባሪዎች እነማን እንደሆኑ በግልፅ ለማወቅ ተችሏል። በጥቅምት ወር በተለያዩ የኦሮሚያ አከባቢዎች የተካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ ዋና አስተባባሪዎች የህወሓት አባላትና ደጋፊዎች ናቸው። የዚህ መሰረታዊ ዓላማ፣ አንደ አቶ ዳንኤል ብርሃኔ አገላለፅ፣ የተቃውሞ ሰልፉ የሚመራው በአዲሱ የኦህዴድ አመራር ውስጥ ሰርጎ በገባ “ከተጠበቀው በላይ ትልቅ በሆነ የህቡዕ ድርጅት” እንደሆነ በመግለፅ በተለይ በኦሮሚያና ሶማሌ ክልሎች ላይ የአስቸኳይ ግዜ አዋጅ ለማወጅ ነበር። ከታች በምስሉ ላይ የሚታየው ፅሁፍ የህወሓቱ ሊቀመንበር ዶ/ር ደብረፂዮን ገብረሚካኤል ለሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው ያቀረቡትን የውሳኔ ሃሳብና የወደፊት አቅጣጫ ነው፡-

አሁን-ያለንበት-ሁኔታ-የኔ-ድምዳሜዎች-ስራ-አስፈፃሚ ገፅ 1-2 (ከዶ/ር ደብረፂዮን ኮምፒውተር ተሰርቆ የወጣ ሰነድ)

ከላይ በተጠቀሰው መሰረት በኦሮሚያና ሶማሌ ክልሎች ላይ የአስቸኳይ ግዜ አዋጅ ለማወጅ የቀረበው የውሳኔ ሃሳብ ከኦህዴድና ብአዴን አመራሮች በገጠመው ጠንካራ ተቃውሞ ምክንያት ውድቅ መደረጉ ይታወሳል። ይህን ተከትሎ ህወሓቶች ከአስራ ስድስት አመታት በፊት የወጣ “የብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት” የሚባል አዋጅ ከተጣለበት አንስተው አመጡ። በድጋሜ የምክር ቤቱን ዝርዝር የአተገባበር ዕቅድና ዓላማ የያዘ ሰነድ አፈትልኮ መውጣቱ ይታወሳል። ይህ ሰነድ በሀገሪቱ የዘር ማጥፋት እየተከሰተ መሆኑን በመጥቀስ ግጭትና አለመረጋጋት ካለባቸው አከባቢዎች የክልል ፖሊሶችን ማስወጣትና የክልሎች ኮሚዩኒኬሽን ኃላፊዎች ስለ ግጭቱ ለሀገር ውስጥና ለውጪ ሚዲያዎች መግለጫ እንዳይሰጡ የሚከለክል ነው።

አሁን-ያለንበት-ሁኔታ-የኔ-ድምዳሜዎች-ስራ-አስፈፃሚ ገፅ 3-4 (ከዶ/ር ደብረፂዮን ኮምፒውተር ተሰርቆ የወጣ ሰነድ)

የብሔራዊ የደህንነት ምክር ቤቱ ሰነድ ይዘት የህወሓቱ ሊቀመንበር ዶ/ር ደብረፂዮን ገብረሚካኤል ለኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ባቀረቡት የውሳኔ ሃሳብ ላይ ተንተርሶ የተዘጋጀ እንደሆነ መገንዘብ ይቻላል። በአጠቃላይ የምክር ቤቱ ዓላማና የተግባር እቅድ በኦህዴድና ብአዴን ተቃውሞ ውድቅ የተደረገው የአስቸኳይ ግዜ አዋጅ በብሔራዊ የደሀንነት ምክር ቤት በኩል ተግባራዊ ማድረግ ነው። ነገር ግን፣ በምክር ቤቱ ም/ሰብሳቢ የሆኑት የመከላከያ ሚኒስቴር ሚኒስት አቶ ሲራጅ ፈጌሳ ባቀረቡት ሪፖርት መሰረት የብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤቱ የታለመለትን ዓላማ ማሳካት እንዳልቻለ ገልፀዋል። ለዚህ ደግሞ አንዳንድ የክልል መስተዳደሮች የምክር ቤቱን ዓላማና ግብ ለማስፈፀም ተባባሪና ፍቃደኛ ባለመሆናቸው ምክንያት እንደሆነ አስረድተዋል።

ከዚያ በመቀጠል አራቱም የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች 17 ቀናት የፈጀ ስብሰባ ማድረጋቸው ይታወሳል። በዚህ ስብሰባ ኦህዴድ እና ብአዴን በአንድ ወገን፣ ህወሓትና የእሱ መጠቀሚያ እየሆነ ያለው ደኢህዴን ደግሞ በሌላ ወገን ሆነው ባደረጉት ፍጭት የመጀመሪያዎቹ ሙሉ በሙሉ አሸንፈዋል። ነገር ግን፣ የስብሰባውን መጠናቀቅ ተከትሎ በኢትዮጲያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢብኮ-EBC) በኩል የተሰጠው መግለጫ ከስብሰባው ውጤት ፍፁም የተለየ እንደነበር ይታወሳል። በእርግጥ መግለጫው ጥሩ የሆነ ፖለቲካ ነክ ድርሰት ወይም ቲያትር እንጂ የስብሰባ መግለጫ አይመስልም። ከተወሰኑ ቀናት በኋላ አራቱ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ሊቀመንበሮች በጋራ በሰጡት መግለጫ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ያሳለፈው ውሳኔ በቴሌቪዥን ከተላለፈው መግለጫ ጋር ለየቅል እንደሆነ በተግባር ተመልክተናል።

ባለፈው ወር የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ለአስር ቀናት ያደረገውን ስብሰባ ተከትሎ ባወጣው መግለጫ የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ የሳለፋቸው ውሳኔዎች ያለ ምንም መሸራረፍ ተግባራዊ እንዲደረጉ መጠየቁን ተከትሎ በመቶች የሚቆጠሩ የፖለቲካ እስረኞች ተፈትተዋል። ሆኖም ግን፣ የኦፌኮ ም/ሊቀመንበር የሆኑት ኦቦ በቀለ ገረባን ጨምሮ አንዳንድ የፖለቲካ እስረኞችን ባለመፈታታቸው ምክንያት ከየካቲት 03/2010 ጀምሮ የገበያና የስራ ማቆም አድማ መጠራቱ ይታወሳል። ይህን ተከትሎ የፌደራሉ መንግስት እነ በቀለ ገረባ ጨምሮ ሌሎች የፖለቲካ እስረኞችን ፈትቷል።

ጥቅምት 03/2010 ዓ.ም እና የካቲት 03/2010 ዓ.ም በተለያዩ የኦሮሚያ አከባቢዎች የተካሄዱት የተቃውሞ ሰልፎች ፍፁም ተመሳሳይ እንደሆኑ ለመገንዘብ ችያለሁ። በመጀመሪያ ደረጃ አዲሱ የኦህዴድ አመራሮችና ለእነሱ ቅርበት ያላቸው ልሂቃን በአምስት ወራት ልዩነት በተመሳሳይ ቀናት የተጠሩት የተቃውሞ ሰልፎች እንዲካሄዱ ፍላጎት አልነበራቸውም። የኦህዴድ ፅ/ቤት ኃላፊ የካቲት 04/2010 ዓ.ም በሰጡት መግለጫ በተለያዩ የክልሉ አከባቢዎች እየተካሄደ ያለው አድማና ተቃውሞ ከዛሬ ጀምሮ መቆም እንዳለበት መናገራቸው ይታወሳል። የክልሉ ፖሊሶችን ጨምሮ በተለያየ ደረጃ የሚገኙ የክልሉ መንግስት ባለስልጣናት ሁኔታዎችን ለመቆጣጠር ጥረት ሲያደርጉ ተስተውሏል። ለምሳሌ በምዕራብ አርሲ ሻሸመኔ ከተማ በተካሄደው ሰልፍ የከተማ ካንቲባዋ በአካል በመገኘት ሰልፈኞችን ሲያነጋግሩና ሲያረጋጉ ተስተውለዋል።

በተመሳሳይ ቀን በወሊሶ ከተማ የተካሄደውን የተቃውሞ ሰልፍ ፖሊሶች በኃይል ለማስቆም ጥረት በማድረጋቸው ምክንያት ከሰልፈኞች ጋር ወደ አላስፈላጊ ግጭት ውስጥ አስገብቷቸው ነበር። ሆኖም ግን፣ በቀጣዩ ቀን (የካቲት 04/2010 ዓ.ም) እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለው የከተማና የአከባቢው ነዋሪዎች ለተቃውሞ አደባባይ መውጣታቸውን ተከትሎ የፖሊስ አዛዡ በአካል ቀርቦ ሰልፈኞችን ይቅርታ እንዲጠይቅ ተደርጓል። ይህን ተከትሎ በዕለቱና በማግስቱ በከተማዋ በተካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ በፖሊሶችና ሰልፈኞች መካከል በጥቅምት 03/2010 ዓ.ም የታየው ዓይነት መግባባት ተፈጥሯል። በመጨረሻም የካቲት 04/2010 ዓ.ም በወሊሶ ከተማ የተካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ ልክ ጥቅምት 03/2010 ዓ.ም እንደተደረገው ፍፁም ሰላማዊ ከመሆኑም በላይ በሀገር ሽማግሌዎች ምርቃት ነው የተጠናቀቀው።

የኦህዴድ አመራሮች ለክልሉ ፖሊሶች ጥብቅ መመሪያ በመስጠት፣ እንዲሁም የሀገር ሽማግሌዎችን በማስተባበር በአምስት ወራት ልዩነት በተመሳሳይ ቀናት የተካሄዱትን የተቃውሞ ሰልፎች በሰላማዊ መንገድ እንዲጠናቀቁ ለማድረግ ጥረት ሲያደርጉ የነበረበት መሰረታዊ ምክንያት አንድና አንድ ነው። ምክንያቱም ህወሓቶች እነዚህን የተቃውሞ ሰልፎች የአስቸኳይ ግዜ አዋጅ ለማወጅ መንደርደሪያ እንደሚያደርጏቸው ጠንቅቀው ያውቃሉ። “የፈሩት ይደርሳል፣ የጠሉት ይወርሳል” እንደሚባለው ኦህዴዶች እንዳይመጣ የሸሹት የአስቸኳይ ግዜ አዋጁ ከስድስት ቀናት በኋላ በቴሌቪዥን በኩል ተመልሶ መጥቷል።

በዛሬው ዕለት ወጣ የተባለው የአስቸኳይ ግዜ አዋጁ ዝርዝር የአፈፃፀም መመሪያ ዶ/ር ደብረፂዮን በኦሮሚያና ሶማሌ ክልሎች ላይ የአስቸኳይ ግዜ አዋጅ ለማወጅ ካቀረበው የውሳኔ ሃሳብ፣ እንዲሁም ከብሔራዊ የደህንነት ምክር ቤት የተግበር ዕቅድ ጋር ፍፁም ተመሳሳይ ነው። ከዚህ በተጨማሪ፣ የካቲት 09/2010 ዓ.ም የታወጀው የአስቸኳይ ግዜ አዋጅ የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ለ17 ቀናት ያካሄደውን ስብሰባ ተከትሎ እንደተሰጠው መግለጫ በኢብኮ በኩል የቀረበ ድርሰት ነው። ምክንያቱም የአስቸኳይ ግዜ አዋጁ የታወጀው በተለይ የኦህዴድና ብአዴን አመራሮች በአዋጁ አስፈላጊነት ላይ ሳይስማሙ ነው።

በመጀመሪያ ደረጃ የሚኒስትሮች ምክር ቤት አባል የሆኑት የፌደራል መንግስት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ቤት ኃላፊ ዶ/ር ነገሪ ሌንጮ ለቪኦኤ በሰጡት አስተያየት “የአስቸኳይ ግዜ አዋጅ ማወጅ የሚያስፈለግበት ሁኔታ አለመኖሩን” ተናግረዋል። ዶ/ር ነገሪ ይህን በተናገሩበት ቅፅበት “ለምን እንደሆነ ባይታወቅም የሚኒስትሮች ምክር ቤት ሚዲያዎችን ለ7፡00 መጥራቱን” የአማራ ክልል ብዙሃን መገናኛ በፌስቡክ ገፁ ዘግቧል። ነገር ግን፣ ከ11፡00 ሰዓት ላይ የምክር ቤቱ ስብሰባ እንዳልተቋጨ በመናገር ሚዲያዎቹ ወደመጡበት እንዲሄዱ ከተነግሯቸው በኋል በምሽቱ የኢብኮ ዜና ላይ የአስቸኳይ ግዜ አዋጅ መታወጁ “በሰበር ዜና” ብለው አቀረቡ።

ከላይ ከተጠቀሰው የዶ/ር ነገሪ አስተያየት እና የአማራ ክልል ብዙሃን መገናኛ ጥቆማ የኦህዴድና ብአዴን ከፍተኛ አመራሮች ስለ አስቸኳይ ግዜ አዋጁ የሚያውቁት ነገር እንደሌለ ያሳያል። ከዚህ በተጨማሪ፣ በትላንትናው ዕለት በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ዞን ከሚገኙ ሴክተር መስሪያ ቤቶች የተወጣጡ ሰራተኞች ስለ አስቸኳይ ግዜ አዋጁ አስፈላጊነት ሲወያዩ እንደነበር ለማወቅ ችያለሁ። በተመሳሳይ በዛሬው ዕለት የአማራ ብዙሃን መገናኛ እኔን ጨምሮ የተለያዩ የዩኒቨርሲቲ ምሁራን በአስቸኳይ ግዜ አዋጁ አስፈላጊነት ዙሪያ አወያይቶናል።

በአጠቃላይ የኦሮሚያና የአማራ ክልል መስተዳደሮች በአስቸኳይ ግዜ አዋጁ አግባብነት ዙሪያ ሕዝቡ ሃሳብና አስተያየት እንዲሰጥ እያደረጉ ነው። በአዋጁ ዙሪያ የራሳቸውን አቋም ለመያዝ ከተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች ጋር ውይይት እያደረጉ ይገኛሉ። በመሆኑም የኦህዴድና ብአዴን አመራሮች በአስቸኳይ ግዜ አዋጁ ዙሪያ ከስምምነት ላይ አልደረሱም። ስለዚህ የአስቸኳይ ግዜ አዋጁ ህወሓት ፍርሃቱን ለማስታገስ በቴሌቪዥን የሚያስነግረው ውሸት ነው። ከላይ በቀረበው የሰነድ ማስረጃ በዝርዝር እንደተገለፀው፣ የአስቸኳይ ግዜ አዋጁ በዶ/ር ደብረፂዮን የተፃፈ የህወሓቶች አሻጥር ነው፡፡


EmbassyMedia - ራብዓይ ግንባር!

Dehai Events