Basic

Goolgule.com: የህወሃትና ኦብነግ የትግል አጋርነት – በንጹሃን ደም ሲታተም አየን!! ድሮ "መደመራቸው" ተረጋገጠ!!

Posted by: Berhane.Habtemariam59@web.de

Date: Wednesday, 08 August 2018

በሚያዚያ 1999 አቦሌ በሚባለው የነዳጅ ጉደጓድ መቆፈሪያ ካምፕ 200 የሚጠጉ የኦጋዴን ነጻ አውጪ ግንባር ታጣቂዎች በድንገት የፈጸሙት ጥቃት አስደንጋጭና አረመኔነት የተሞላበት ነበር። በወቅቱ ዘጠኝ ቻይናዎችን ጨምሮ በድምሩ ሰባ አራት ንጹሃን ህይወት አለፈ።

በወቅቱ ጥቃቱ የተፈጸመው በሌሊት ሁሉም በተኙበት ሲሆን ግናብሩ ንጹሃንን ከጨፈጨፈ በኋላ ሰፊ መነጋገሪያ የነበረው ጉዳይ እንዴት ጥበቃው ላላ? እንዴት መከለከያና ደህንነት መረጃ አልባ ሆኑ? የሚለው ነበር። በዚህን ወቅት አሁን አገር የሚያተራምሰው ወሮበላ አብዲ ኢሌ የክልሉ የጸጥታ ሃላፊ ነበር።

የሚገርመው ይህንን አረመኔነት የተመላበት ድርጊት የፈጸሙት አውሬዎች ተይዘው በክልሉ ፍርድ ቤት ሞት ተፈርዶባቸው ወደ ዝዋይ ማረሚያ ቤት እንዲዛወሩ ተደርጎ ፍርዱ ሳይፈጸምባቸው ዓመታትን አስቆጠሩ።

ምንጩ በውል በማይታወቅ ገንዘብ በዝዋይ ከተማ ትልቅ ቪላ ተከራየትው በጋሪ ሙሉ ምግብ እየተጋዘላቸው ዝዋይ ሲቀለቡ የነበሩት ነብሰ በላዎች፣ ፍርዱ ለዓመታት ተግባራዊ ያልሆነበት ምክንያት ሳይገለጽ ህወሃት/ኢህአዴግ ከኦጋዴን ነጻ አውጪ ግንባር አንድ የጎሳ አፈንጋጭ ክንፍ ጋር መስማማቱን ይፋ አደረገ።

በወቅቱ በሸራተን ሆቴል በተሰጠ መግለጫ ስለ እነዚሁ ጨፍጫፊዎች ጉዳይ እና የፍርድ አፈጻጸም ተጠይቆ አባይ ጸሃዬ “ስምምነት ሲባል ሁሉን አቀፍ ነው” ሲል ፍርደኞቹ ነጻ እንዲሆኑ ማድረግ አንዱ የስምምነቱ አካል መሆኑንን ነገረን። ፍርዱ ሳይተገበር ከሰባት ዓመት በላይ የቆየበት ምክንያት ግን እስካሁን እንቆቅልሽ ነው። በተለይም ህወሃትና ደም ካላቸው የጠበቀ ግንኙነት አንጻር!!

እዚህ ላይ የሚታየው ዋናው ጉዳይ ስምምነት ለማውረድ ሙከራ መደረጉ ሳይሆን ስምምነት የሚደረግባቸው፣ ስምምነት እንዲደረግ የሚፈለግባት ወቅት፣ ስምምነቱ ተቋረጠ የሚባልበት ምክንያትና ወቅት እየጠበቀ የእርቁ ጅማሬ መፍረሱ የሚታወጅበት አካሄድ ነው። ይህ በራሱ ምርምር የሚያሻው ጉዳይ ሲሆን ባጭሩ ግን የተወሰኑ ጉዳዮችን ማንሳት ይቻላል። (ኦብነግና ኢህአዴግ ንግ ግር አቆሙ በሚል ርዕስ ጎልጉል የዛሬ ስድስት ዓመት አካባቢ ያቀናበረው ዘገባ እዚህ ላይ ይገኛል።)

“ኢትዮጵያ ጨቆነችን” በሚል ስም እንደ ካኔቴራ እየቀያየረና የተሻለ የሚባል አስተሳሰብ ያላቸውን አመራሮች እየበላ “መንግስት” ለመሆን የበቃው ራሱን የትግራይ “ነጻ አውጪ” ብሎ የሚጠራው ቡድን ሲጀመር ሶማሌ ሞቃዲሾ ውስጥ እንዳሻው ሲናኝና የሶማሌ ፓስፖርት በመጠቀም ከወዲያ ወዲህ ሲል የኖረ ለመሆኑ ማስረጃ አይሻም።

መለሰ ዜናዊ በሶማሌ ቆይታው የሶማሌ የጎሳ ፖለቲከኞችን ከማደራጀት ጀምሮ ከተለያዩ ዛሬ “አሸባሪ” ተብለው ከተፈረጁ ድርጅቶች ጋር መስተጋብር እንደነበረው በርካታ የሶማሌ ዜጎች ይመሰክራሉ። የዚህ በመለስ መሰበካቸውን የሚናገሩ የቦሌ ክፍለ ከተማ ነዋሪ የሆኑ የሶማሌ ተወላጆች ህያው ምስክር ናቸው።

ሶማሌያን የገቢ ምንጭ እና የስልጣን ማስከበሪያ መደራደሪያ በማድረግ ሃያ ሰባት ዓመት ህዝብ እየቆላ፣ አገር እየዘረፈ፣ ድሆችን እያሳደደ፣ ስልጣንን በብቸኛነት ይዞ እንዳሻው ሲፈነጭ የቆየው ህወሃት፣ ሶማሌ ላይ የዘረጋው የስልጣን ማቆያ ፕሮጀክትና የዶላር እርሻ ጥርጣሬ እንዳይገባው፣ መልኩ የተስተካከለ ገጽታ እንዲያዝ የቅርብ ወዳጆቹ የሆኑትን የኦብነግ ሰዎች ይጠቀምባቸዋል። ጌቶቻቸው ሳይቀሩ “እንደ ህወሃት ያታለለን የለም” ማለታቸው ዝም ብሎ በምርጫና በዴሞክራሲ ግንባታ በደረሰበት ክሽፈት አይደለም። እነሱ ስለ ዴሞክራሲና ህዝብ መብት ደንታ የላቸውምና።

የኤርትራው መሪ ኢሳያስ አፈወርቅ “ጥምብ አንሳዎች” ሲሉ የሚሰነፍጥ የስድብ ኒውክሌር ካወረዱባቸው በኋላ “ጨዋታው አብቅቷል” ማለታቸው፣ የሚስተር ያማማቶ ሶማሌ ላይ አምባሳደር ሆኖ መሾም የቀደመው የወያኔ ድራማ መንተብ የሚያሳይ እንደሆነ በዘርፉ የተማሩ የገለጹት እውነት ከዚሁ እውነት የሚቀዳ ነው። በተጨማሪም አቶ ኢሳያስ እንዳለው በቀጠናው የተቀየሰውን አዲስ ስትራቴጂ ከወያኔ ልኬት ውጪ ነው።

እናም የጌቶቻቸውን ኪስ ለማውለቅ ቆዳቸውንና ስልታቸውን የሚቀያይሩት የወያኔ ቁንጮዎች፣ ኦብነግን ለዚሁ ዓላማ በሶማሌና በአገር ቤት የተለያየ ስም እየሰጡ፣ “እኛ ይህንን ቦታ ስንለቅ አንተ ግባና ተቆጣጠረው” እያሉ፣ በምስኪን የመከላከያ ሰራዊት አባላት ደምና አጥንት ዶላር አፍሰዋል። ከዚሁ በሶማሌ ምድር ህወሃት በሚሰራው ሽፍጥ የተማረረው የሰላም አስከባሪ ሃይል /አሚሶም/ ከእነሱ ጋር መስራት አለመቻሉን በተደጋጋሚ ሲገልጽ መቆየቱ የሚዘነጋ ብቻ ሳይሆን ከላይ የተባለውን የሚያጠናክር ቁልፍ ጉዳይ ነው። (“ህወሃት በሚያኮርፍባቸው የሶማሊያ ‹አሸባሪ› ድርጅቶች ይጠረጠራል” በሚል ርዕስ የተዘጋጀውን ዘገባ ለማንበብ እዚህ ላይ ይጫኑ)

ዛሬ በገሃድ በንጹሃን ደምና ስቃይ፣ በእምነት ቤቶች መንደድ ህወሃትና ኦብነግ ለምን ይደንሳሉ?

በቆየ ትሥሥር፣ የስም ዝምድና፣ በመገንጠል የዓላማ አንድነት ውህድ የሆኑት ኦብነግና ህወሃት ዛሬ የንጹሃን ደም ሲፈስ፣ ነፍሰጡሮች ታግተው ሲያነቡ፣ እርጥብ አራሶች የሚያጠቡት ነጥፎባቸው ሲሰቃዩ፣ ያልጠነከሩ እመጫቶች መከራን ሲጋቱ፣ የድሆች ንብረት ጭልፋና ድስት ሳይቀር ሲዘረፍ፣ ምንም የማያቁ ለፍቶ አዳሪዎች ታገተው ሲቀሉ፣ ቤተ እምነቶች ሲጋዩና የሃይማኖት መሪዎች ሲቃጠሉ ህወሃት በትግራይ መንግስት ስም፣ ረብጣ ብር በሚያፈስላቸው የሚዲያ አርበኞቹ፣ ሚስጥሩ ሳይገባቸው እንደ ቆርቆሮ በሚጮሁ አማራጭ አልባ ወዳጆቹ አማካይነት እልልታ ማሰማቱ ዛሬ በተጀመረው ለውጥ ከተፈጠረ ቅሬታ ሳይሆን የቀደመ ውጥን ውጤት መሆኑንን መረዳት አግባብ ይሆናል።

አንድ አገርን በነጻ አውጪ ስም እየተጠራ ሲመራ የነበረ ቡድን በምስኪኖች መካከል መሽጎ በሕዝብ ስም እንዲህ ያለውን ተግባር ሲፈጽም ዝም መባሉ ብቻ ሳይሆን አብረው የሚደንሱና የሚያሽካኩት ዜጎች ጉዳይ ያሳዝናል።

ላለፉት አስርት ዓመታት በሶማሌ ክልል መሪነት የተቀመጠው አብዲ ኢሌ የሚባል ግብዝ የራሱ ክልል ነዋሪዎች እንዳሉት በክልሉ ፖሊስ፣ ዳኛ፣አቃቤ ህግ፣ የገንዘብ ሚኒስትር፣ ፈላጭና ቆራጭ ሆኖ ህዝብ ላይ ሲጨፍር ህወሃት የት ነበር? በእርግጥ ተቆርቋሪነቱ ለሶማሌያ ክልል ህዝብ ከሆነ የሶማሌ ክልል ነዋሪዎች ሲደፈሩ፣ ሲገደሉ፣ በግንብ በታጠረ ማጎሪያ በሙቀት ሲነፍሩ፣ ብልታቸው ሲኮላሽ፣ አንድ ጉድጓድ ውስጥ በጅምላ  ሲቀበሩ … ህወሃት የት ነበር ?

እዚህ ላይ ስለ ወንድሙ ኦጋዴን ነጻ አውጪ ግንባር አሽከርነት እና ዝምድና በማንሳት ከላይ ቀደም ሲል የተነሳውን እናጠናክር። አብዲ ኢሌ ያዘጋጃቸው ወጠጤዎችና “ባለ ራዕዩ” የደራጀለት የታጠቀ ሃይል በጥምረት በጅጅጋና በተለያዩ ከተሞች አስነዋሪ ድርጊት መፈጸማቸውን ተከትሎ የመከላከያ ሃይል ወደ ከተማዋ ሲገባ የትግራይ ክልላዊ መንግስት የተቀውሞ መግለጫ አወጣ። ወንድሙ ኦብነግ ተከተለ።

እዚህ ላይ ልብ ሊባል የሚገባው ጉዳይ። በሶማሌ ክልል ተወላጆች በቡድን ሲደፈሩ፣ ቶርቸር ሲደረጉ፣ ሲገደሉ፣ በጅምላ በአንድ ጉድጓድ ሲቀበሩ የነበሩት “ኦብነግ ናቸሁ፣ ለኦብነግ ሰዎች ምግብ ሰጥታችኋል፣ የኦብነግ ሰዎችን ደብቃችኋል፣ የኦብነግ ሰዎችን ጠቁሙ… ” በሚል ጉዳይ ብቻ ነው። የዖጋዴን እስር ቤት ምሥጢርም ከኦብነግ ጋር የተያያዘ ነው። ኦብነግ ሳይጠቀስ ያልተከሰሰና እዚያ እስርቤት ያልገባ አለ ለማለት ያስቸግራል። ይህ እውነታ እያለ ነው ኦብነግ የአብዲ ኢሌና የሕገመንግሥት አተረጓጎም አሳስቦት መግለጫ ያወጣው።

አብዲ ኢሌ መሪ ሆኖ ከመመረጡ በፊት ከህወሃት የአፈና ሃይሎች ጋር በመሆን የክልሉ የጸጥታ ሃላፊ ሆኖ የማሰቃያ ስልጠናዎችን ተግቷል። ሰለጥኗል ለማለት ነው። ተግቷል ያልነው የመሰልጠን አቅምም ሆነ ተፈጥሮ የሌለው ደንቆሮ በመሆኑ ነው። እዚህ ላይ አንድ ጥያቄ እናንሳ ስለምን ህወሃት አንድ ስሙን መጻፍ የማይችል የዓለም ሁሉ ደናቁርት ድምር ውጤት የሆነ ሃውልት በሶማሌ ክልል ላይ ሰየመ? ድራማው ነዋ!! ሌላ ምን ሊሆን?

የሶማሌ ክልል ነዋሪዎች በኦብነግ ስም ይህ ሁሉ መከራ እየደረሰባቸው አብዲ ኢሌ እንዳይነካ ተሽቀዳድመው ከትግራይ ክልል ቀጥሎ የተቃውሞ መግለጫ ማውጣታችው ድራማው ማሰብ ለሚችሉ ብቻ ሳይሆን ለማንም ፍንትው ብሎ እንዲታይ አስችሏል። ሌሎች ስለመደመር ዛሬ ስናወራ እነሱ (ህወሃትና ኦብነግ) ድሮ ተደምረዋል። አሁን “ተደመሩ፣ የሚያዋጣው መደመር ብቻ ነው” ሲባሉ “እኛ ድሮ ተደምረናል” የሚል ምላሽ በግልገሎቻቸው አማካይነት ሲሰጡ የገባቸው ስንቶች ይሆኑ?

ሌላ ጉዳይ እናንሳ በኦጋዴን ነዳጅና የተፈጠሮ ጋዝ መገኘቱን ተከትሎ ተሸቀዳድሞ ሂሳብ ያሰላውና የነዳጅ ማውጣቱን ስራ “አጨናግፋለሁ” ያለው ኦብነግ ነው። ህወሃቶች በጭፍሮቻቸው አማካይነት ደግሞ “ነዳጁን ያወጣነው እኛ ነን” በሚል መፎከር ጀመሩ። ዛሬ ጥገኘት ለመጠየቅ አሜሪካ የገባው ዳንኤል ብርሃኔ የመከላከያ ሰራዊት ወደ ሶማሌ ክልል መግባቱን ሲቃወም መጀመሪያ ያነሳው የነዳጁን ጉዳይ ነው። እንደ ፌስቡክ ተከፋዩ ዳንኤል ከሆነ በክልሉና በፌደራል መንግስት ደረጃ ጸብ የተነሳው በነዳጁ የፐርሰንት ክፍፍል የተነሳ ነው።

ድሬደዋ ያደገው ዳንኤል ከተባበሩት ኢሜሬትስ በስተቀር እነ ቱርክ ገብተው ሰላም እንዲያስከብሩ እስከ መጠየቅ ደርሷል። ሌሎችም በስም የሚታወቁ የህወሃት ጭፍራዎች ተንጫጭተዋል። እዛው አብዲ ኢሌ ቢሮ መሆናቸውን በመግለጽ “መከላከያና ፌደራል ፖሊስ ከጅጅጋ ወጡ፣ የክልሉ ልዩ ሃይል ከተማዋን ተቆጣጥሯል። ፕሬዚዳንቱ ሰላም ናቸው” እያሉ ተከፍሏቸው በሚጨፍሩበት ፌስቡክ ያለ ሃፍረት ምስላቸውን እየለጠፉ በንጹሃን ደም ላይ ሲያሽካኩ አይተናል። ማንም ምንም አለ ግን በስተመጨረሻ አብዲ ኢሌ ተባሯል። በዓለም አቀፍ የወንጀለኞች ችሎት፣ እንዲሁም በአገሪቱ ህግ ይዳኛል። ይህ እውን ይሆናል።

የሳንቲም አባዜና ሚዲያ

አሁን አሁን የሚታየው “የመገናኛ ዘዴዎች” አካሄድ ከጅጅጋው ቀውስ ባልተናነሰ አሳዛኝ ነው። መረጃን ለማዳረስ የሚደረገው ጥረት በጎ ሆኖ ሳለ፣ የሚመሰገንና ድጋፍ የሚያሻው መሆኑ እሙን ቢሆንም በተጻራሪው ሃፍረትም የተሞላው ነው።

ታቅዶ፣ ተወጥኖና ከስትራቴጂ እየተቀዳ የሚሰራጭን መርዝ ለይቶ የማጣጣም ነገር እጅግ በጣም ጥቂት፣ በጣም ጥቂት፣ እጅግ ጥቂት ከሆኑ በስተቀር አይታየም። የተለቀለቀውን ሁሉ የማግበስበስ ጉዳይ ገኗል። የሰዎችን ንግግር በመቆራረጥ ለሌሎች አስበው ለሚሰሩት እንዲመች በማድረግ የመቸርቸር  ገበያ መር “ጋዜጠኝት” ሰፍኗል።

በብዛት እንደሚታየው ጽሁፍን አንብቦ እንኳን መለጠፍ የለም። ዝም ብሎ ማግበስበስ። ቆርጦ መለጠፍ። ማሰራጨት። ማባዛት፣ እንዲሁ ሳንቲም ለመልቀም ነገሮችን ማጯጯህና በርካታ ጎብኚ በመሳብ ማስታወቂያ ማግኘት ብቻ አጀንዳ የሆነ ይመስላል። ደግሞም ነው። ይህ የደመ ነፍስ ተግባር አንድ ካልተባለና ሙያዊ መሆኑ ቀርቶ ቢያንስ ወደ ህሊና ሚዛን መሸጋገር ካልተቻለ አደጋው እጅግ የከፋ እንደሚሆን ጥርጥር የለውም።

በማህበራዊ ገጾች፣ በተለያዩ ድረ ገጾች የሚታየው ይህ ስሜትን ያልገዛና በስትራቴጂ ለሚመሩት ክፉዎች መረብ የሚዳርግ አካሄድ አገራችንን እንወዳለን፣ ለውጡን እንደግፋለን፣ ለአዲሱ ስርዓት መጠናከር እርዳታ እናደርጋለን በሚሉ ወገኖች አማካይነት ሊታረቅ ይገባል።

አንባቢውም ቢሆን ዝም ብሎ ከማግበስበስ ሊቆጠብና በሰበር ዜና ከመጦዝ ለራሱ ልጓም ሊያበጅ እንደሚገባ ማወቅ አለበት። በስማ በለው መረጃ መደነባበር፣ እንዲሁም እሱን እየተቀበሉ በየማህበራዊ ገጹ መበተን ጥንቃቄ እንደሚያሻው ሊያውቅ ይገባል። መረጃን መቀባበልና መጋራት ደግ ተግባር ቢሆንም ማስተዋልና መርዙን ሃሳብ ከቀናው መለየት አግባብ ነው። አለያ ነገ እናዝናለን። ሃዘናችን ደግሞ ቀላል አይሆንም። አገርን የሚያድንና የሚታደግ ህዝብ እንጂ ሰራዊት አይደለምና አገራችንን ልንጠብቅ ይገባል።

ከዚሁ ጋር በተያያዘ በቨርጂኒያ የህወሃት ደጋፊዎች አዲስ ሚዲያ በመክፈት አገር ቤት በተጀመረው ለውጥ ላይ ዘመቻ ለመክፈትና አማራንና ኦሮሞን መልሶ ለማናከስ እቅድ ይዘዋል። ዳንኤል ብርሃኔ ለዚሁ ተግባር እዛ የሚገኝ ሲሆን ሆን ብሎ ፌስቡክ ላይ በሚጽፋቸው ጉንተላዎች ተበሳጭተው መልስ የሚልኩለትን በማሰባሰብ ጥገኝነት ለመጠየቅ በዝግጅት ላይ መሆኑን ጉዳዩን የሚያውቁ እየገለጹ ነው።

እንደነዚህ ክፍሎች ገለሳ ጉዳዩ ከወዲሁ ዘመቻ ያስፈልገዋል። አስተባባሪዎች ሊመደቡ ይገባል። በፌስቡክ ገጹ ላይ አግባብ ያልሆነ ጉዳይ የምትጽፉ ታቀቡ ሲሉ መክረዋል።

ህወሃት መሰሪ፣ ጸረ ኢትዮጵያና አሸባሪ ቡድን ነው። በበረሃ በርካታ ውንብድና ሲፈጽሙ የኖሩት ወሮበሎች አገር በግፍ ሲገዙም ከዚያው የውንብድና አስተሳሰብ ሳይወጡ ነበር። ይህንኑ የውንብድና አስተሳሰባቸውን ለመተግበር ተመሳሳይ ከሰው ስብዕና ውጪ የሆኑ እንደ አብድ ኢሌ ዓይነቶችን በህዝብ ሲቀልዱ ኖረዋል። አሸባሪዎች ሆነው አሸባሪነትን ዋንኛ የድራማቸው ርዕስ አድርገው ብዙ ተውነዋል። ሁኔታዎች እዚህ ደርሰው አጣብቂኝ ውስጥ ሲገቡ በገሃድ ፍንትው ብሎ ታየንን እንጂ ኦብነግም ሆን አልሸባብ ራሳቸውን ችለው ለዓላማ የሚታገሉ ቡድኖች ሳይሆኑ ህወሃት ጠፍጥፎ የሠራቸው የራሱ ዓላማ ማስፈጸሚያ የድርጅት ሮቦቶች ናቸው። የሰሞኑ ክስተት ይህንን ያላንዳች ጥርጥር አረጋግጧል። መፍትሔው ደግሞ ህወሃት ሌላ የድርጅት ሮቦት በሌላ መልኩ ሳትፈበርክ እንደ መሪዋ ሥርዓተ ግብዓቷን ማፋጠን ነው። ህወሃት ሲያከትምላት የፈለፈለቻቸው ድቃዮችም ህይወት ዓልባ ይሆናሉና። ለዚህ ተግባራዊነት የሕዝብ የፈረጠመ ጡንቻ ያስፈልጋል። (ፎቶዎቹ ከኢንተርኔት የተገኙ ሲሆን በጎልጉል የተቀናጁ ናቸው)


7ይ ክፋል: ማዕበል ስርሒት ፈንቅል - የካቲት 1990 - ሰነዳዊት ፊልም| sirihit fenkil 1990 - part 7 - ERi-TV Documentary

Dehai Events