Dehai News

Ethsat.com: የህወኃትና ኢህአዴግ ከፍተኛ ሥራ አስፈጻሚና የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ አቶ አባይ ጸሀዬ የመንግስትንና የፓርላማውን አሠራር አጠንክረው ነቀፉ።

Posted by: Berhane Habtemariam

Date: Monday, 03 April 2017

የህወኃትና ኢህአዴግ ከፍተኛ ሥራ አስፈጻሚና የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ አቶ አባይ ጸሀዬ የመንግስትንና የፓርላማውን አሠራር አጠንክረው ነቀፉ።
April 3, 2017
Watch and listen these-

ESAT DC Morning News Mon 03 Apr 2017

https://ethsat.com/2017/04/esat-dc-morning-news-mon-03-apr-2017/

ESAT Daily News Amsterdam April 03,2017

መጋቢት ፳፭ (ሃያ አምስት)ቀን ፪፲፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- እምነት ያጣንበት ሚኒስትር ዳግም እየተሾመ ነው ያሉት አቶ አባይ፤ የመንግስት አሠራር ካልተቀየረ ይች ሀገር በእሳት ትቃጠላለች ሲሊ አስጠንቅቀዋል።

ኢሳት በደረሰው የድምጽ መረጃ ላይ በፓርላማው የተለመደ የደቦና የጥድፊያ አሰራር ትችት የሰነዘሩት አቶ አባይ፤ ሹመትና በጀት ያለብስለትና ያለ እምነት በጥድፊያና በዘመቻ እየጸደቀ አፈጻጸም ላይ ከፍተኛ ችግር ማስከተሉን ጠቁመዋል።

ቋሚ ኮሚቲው ከአስፈጻሚው የመጣውን ማጽደቅ ሥራው ቢኾንም ኮሚቴው ብቃት ኖሮት ወይም ገብቶት ነው ወይ የሚያጸድቀው?”በማለት የጠየቁት አቶ አባይ ፣በተለይ ሹመትና በጀት እዚህ ሀገር ዝም ብሎ ነው የሚጸድቀው ብለዋል።

“አሜሪካም አብላጫ ውንበር ያለው ገዥ ፓርቲ ያቀረበው ህግና በጀት ነው የሚጸድቀው።ሆኖም እነሱ እንደኛ በሰዓታት አይደለም የሚያጸድቁት።አገላብጠው በደንብ ፈትሸው ነው እሚያጸድቁት” ያሉት አቶ አባይ፤ “የራሳቸው ፓርቲ ያስመረጠው ፕሬዚዳንት ያቀረበውን ጭምር በደንብ አገላብጠው አይተው እንጂ የሚያጸድቁት እንደኛ ዝም ብለው አይፈርሙም”ብለዋል።

አክለውም እኛም ጋር ይህ እንዲደረግ ድፍረቱ ካለ መጀመሪያ መስተካከል ያለበት ኢህአዴግ ከኢህአዴግም ካቢኔውና ሥራ አስፈጻሚው ነው ብለዋል። ይሁንና የኢህአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ጸረ ዲሞክራሲ የተጠናወተውና ጸረ ዲሞክራሲ የገነገነበት ነው ያሉት የህወሃቱ መስራች፤ “ ይህ የኔ አስተያዪት ሳይሆን በጥቅል ተሀድሶው የደረስንበት ድምዳሜ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።

“አመራሩ እንኳን ያቀረብከውን ሹመትና በጀት አልተቀበልንህም ሲባል ጠንከር ያለ ጥያቄ ሲቀርብለት የሚያኮርፍ፣ የሚያንገራግርና አካኪ ዘራፍ የሚል ነው ”በማለትም የሥራ አስፈጻሚውን አምባገነንነት በግልጽ ነቅፈዋል።

“በጥልቅ ተሀድሶው ራሳችንን በህግና በዲሞክራሲያዊ ተቋማት አገዛዝ ካላስገዛን ጸረ ህዝብ ፓርቲ በመሆን ወደ ጸረ ህዝብ መንግስት እንቀየራለን የሚል መደምደሚያ ላይ ነው የደረስነው።” ያሉት አቶ አባይ ጸሀዬ፤ “እንኳን በኛ የኪራይ ሰብሳቢነት በሞላበት በሰለጠኑት ሀገራትም አስፈጻሚው በህግና በተቋማት ካልተያዘ ይፈነጫል፣ይባልጋል።እልም ያለ አምባገነን ይሖናል።”ብለዋል።

አያይዘውም “በመሆኑም የሚያጠፋ አካል ይመከር፣ ይስተካከል፤ ሆኖም የማይመከርና የማይስተካከል ከሆነ የሚወገድበትና ከዚያው ፓርቲ ሌላ ግለሰብ የሚተካበት አሰራር የሚከተል ምክር ቤት ሊሆን ይገባል”ሲሉ ሀሳብ አቅርበዋል።

አቶ አባይ በመቀጠልም፦”ይህች ሀገር እንዳትፈርስ፣ወደ ትርምስ እንዳትገባ ከተፈለገ መፍትሔው እሱ ብቻ ነው። አለበለዚያ ይች ሀገር በእሳት ትቀጣጠላለች።ይህን ኢህአዴግ ያውቃል።ህዝብም ያውቃል”” በሁለትና በሶስት ወር ውስጥ ምን አይነት እሳት መቀጣጠል ጀምሮ እንደነበር ዐይተነዋል”ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

“እናውቀዋለን እኮ። በየአምስት ወሩና ስድስት ወሩ የሚቀደድ በርካታ ህግኮ ነው እዚህ አገር ያለው” ያሉት አቶ አባይ፤ “ ሥራ አስፈጻሚው ወይም ካቢኔው አንድን አዋጅ ላከ ማለት ያለቀለት መጽሀፍ ቅዱስ ወይም ቁርአን ማለት አይደለም። መቀየር ካለበት ሊቀየር ይገባል ”ብለዋል።

በዚሁ ኢሳት እጅ ውስጥ በገባው የድምጽ መረጃ “ሦስቴና አራቴ ያደረቀንና ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ድረስ አቤቱታ ያቀረብንበት ሚኒስትርና የቢሮ ኃላፊ እንደገና ለምንድነው በሹመት የሚቀጥለው?”በማለት ሲጠይቁ የሚደመጡት አቶ አባይ “እምነት አላሳደርንበትም ያልነው አካል ይወገድ፤ አለበለዚያ በሚዲያ እናውጀዋለን” ሲሉም አስጠንቅቀዋል።

****************************************************************************
 
በጎንደር ከተማ አንድ ሆቴል ውስጥ ጥቃት ተፈጽሞ በሰዎችና በንብረት ላይ ጉዳት ደረሰ

ኢሳት (መጋቢት 25 ፥ 2009)

April 3, 2017

በጎንደር ከተማ ፍሎሪዳ ኢንተርናሽናል ሆቴል ላይ ቅዳሜ ምሽት የቦምብ ጥቃት ደረሰ። ጥቃቱ የተፈጸመበት ባለሶስት ኮከብ ሆቴል በአብዛኛው የወታደራዊ አዛዥ ጄኔራሎችና ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት የሚያርፉበት እንደኾነ እማኞች ለኢሳት ገልጸዋል።

ማራኪ ተብሎ በሚታወቀው የጎንደር ዩኒቨርስቲ አካባቢ በሚገኘው በዚሁ ሆቴል የተፈጸመውን ጥቃት ተከትሎ ሶስት ሰዎች መቁሰላቸውን ለማወቅ ተችሏል። ለጥቃቱ እስካሁን ሃላፊነት የወሰደ አካል የለም።

በዚሁ በፍሎሪዳ ኢንተርናሽናል ሆቴል የደረሰው ጥቃት በኢትዮጵያ ሰዓት አቆጣጠር ከምሽቱ ሶስት ሰዓት ላይ እንደሆነ የተገለጸ ሲሆን፣ በጥቃቱ ሶስት ሰዎች ቆስለው የሆቴሉ መስታዎቶችም መሰባበራቸው ታውቋል። እንደ አይን ምስክሮች ገለጻ በፍሎሪዳ ኢንተርናሽናል ሆቴል የወታደራዊ ዕዙ (ኮማንድ ፖስት) ጄኔራሎችና የመንግስት ባለስልጣናት በአብዛኛው የሚያርፉበትና ትዕዛዝ የሚሰጡበት ስፍራ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል። አካባቢው አደጋኛ ቀጠና ተብሎ በከፍተኛ ጥበቃ የነበረበት ስፍራ መሆኑም ተገልጿል።

በፍሎሪዳ ኢንተርናሽናል ሆቴል ጎንደር ከተማ የተፈጸመው የቦንብ ጥቃት ተከትሎ በርካታ የአካባቢው ሰዎችና መንገደኞች መታሰራቸውን የአይን እማኞች ገልጸዋል።

በጎንደር ከተማ ፍሎሪዳ ኢንተርናሽናል ሆቴል ለተፈጸመ የቦምብ ጥቃት እስካሁን ሃላፊነቱን የወሰደ አካል የለም። ይህም ሆኖ ግን በህዝቡ ውስጥ በአገዛዙ ላይ ከፍተኛ ቅሬታ በመኖሩ ምናልባትም ጥቃቱ የደረሰው በስርዓቱ ላይ ተቃውሞ ያላቸው አካላት ሊሆኑ እንደሚችሉ ግምቶች አሉ።

በጎንደር ከተማ የሚገኘው የፍሎሪዳ ኢንተርናሽናል ሆቴል ባለቤት አቶ አባቡ ሃሽም የሚባሉ ግለሰብ ናቸው። በሆቴሉም በርካታ መንግስታዊ ዝግጅቶች የሚካሄዱበት እንደሆነ ታውቋል።

መንግስት በመጪው ሚያዚያ ወር የከተሞችን ቀን በጎንደር ከተማ ለማክበር ቀን ቆርጦ ዝግጅት ላይ ባለበት ወቅት ጥቃቱ መፈጸሙ ታውቋል።

*****************************************************************************

ከዋልድባ ገዳም ተቃውሞ ጋር በተገናኘ 39 የገዳሙ መነኩሴዎች መታሰራቸው ተገለጸ

ኢሳት (መጋቢት 25 ፥ 2009)

April 3, 2017

https://ethsat.com/wp-content/uploads/2017/04/waldiba.jpgበቅርቡ ለእስር የተዳረጉት የዋልድባ ገዳም መነኩሴ አባ ገብረየሱስ ወደ ማዕከላዊ እስር ቤት መወሰዳቸውንና የስቃይ ሰለባ ይሆናሉ የሚል ስጋት እንዳደረበት የዋልድባን እንታደግ ማህበር ሰኞ አስታወቀ። በአጠቃላይ 39 የዋልድባ ገዳም መነኩሴዎች መታሰራቸውንም መረዳት ተችሏል።

አባ ገብረየሱስ የዋልድባ ገዳሙ ለልማት መነካት የለበትም በማለት ሲያሰሙ የቆዩትን ተቃትሞ ተከትሎ በመንግስት የጸጥታ ሃይሎች ክትትል ሲደረግባቸው ቆይቶ ከሁለት ወር በፊት ታፍነው መወሰዳቸውን መዘገባቸው ይታወሳል።

ከአንድ ወር በላይ የገቡበት ያልታወቀው አባ ገብረየሱስ ከቀናት በፊት ወደ ማዕከላዊ የምርመራ እስር ቤት መግባታቸው መረጃ እንደደረሰባቸው የዋልድባን እንታደግ ማህበር አባላት የሆኑት አቶ ሳምሶን ታፈሰና አቶ ዳምጠው አየለ ከዜና ክፍላችን ጋር ባደረጉት ቃል-ምልልስ አስረድተዋል።

ገዳሙ በልማት ስም መነካት የለበትም በማለት ለአመታት ተቃውሞን ሲያሰሙ የነበሩት መነኩሴ በቁጥጥር ስር በዋሉ ጊዜ ከፍተኛ ድብደባ እንደተፈጸመባቸው የማህበሩ አባላት አክለው ገልጸዋል።

አባ ገብረየሱስ፣ ገዳሙ መነካት የለበትም ያሉትን አቋም በተመለከተ በተለያዩ ጊዜያት ለኢሳት እንዲሁም ለአሜሪካ ድምፅ የአማርኛው ፕሮግራም ቃለ-መጠየቆችን ሲሰጡ መቆየታቸው ይታወሳል።

የዋልድባን ገዳም መነኩሴ በጸጥታ ሃይሎች ሲደረግባቸው ከነበረ ክትትል ለማምለጥ ራሳቸውን ለአምስት አመት ያህል ተሰውረው መቆየታቸውም ተመልክቷል።

የዋልድባን እንታደግ ማህበር መነኩሴው በማዕከላዊ የምርመራ እስር ቤት ቆይታቸው የሰብዓዊ መብት ጥሰት ይፈጸምባቸው የሚል ስጋት እንዳደረበት ገልጿል።

የኢትዮጵያ ኦሮቶዶክስ ተዋህዶ የእምነት ተከታዮች መነኩሴ ለህዝብ እና ለሃይማኖቱ ጥቅም መከበር የከፈሉትን መስዋዕትነት ግምት ውስጥ በመክተት ከጎናቸው እንዲቆምና አጋርነቱን በተለያዩ መልክ እንዲገለጽ የማህበሩ አባላት ጥሪን አቅርበዋል።

የስኳር ኮርፖሬሽን በዋልድባ ገዳም አካባቢ የስኳር ፋብሪካን ለመገንባት በያዘው እቅድ ገዳሙ በልማቱ ስራ እንደሚነካ ለገዳሙ አሳውቆ እንደነበር ይታወሳል። ይህንኑ መረጃ ተከትሎ አባ ገብረየሱስ ለዘመናት የቆየው ገዳም በምንም ሁኔታ ሊነካ አይገባም በማለት በአደባባይ ለመታት ሲያስተጋቡ ቆይተዋል።

የአባ ገረየሱስ መታሰርን ተከትሎም 39 መነኮሳት ተመሳሳይ ተቃውሞን ስታካሄዱ ነበር ተብለው በቁጥጥር ስር መዋላቸውንም ለመረዳት ተችሏል።


EmbassyMedia - ራብዓይ ግንባር!

Dehai Events