Dehai News

Goolgule.com: የነፃነት ኃይሎች ጥቃት ከዳር ወደ መሀል!

Posted by: Berhane Habtemariam

Date: Wednesday, 03 May 2017

የነፃነት ኃይሎች ጥቃት ከዳር ወደ መሀል!

 
  • ጎንደርና ባህርዳር ከተማ ውስጥ በሁለት ወር ብቻ 9 የቦምብ ፍንዳታ ደርሷል!
  • “ህወሃት የሰሜን ምዕራብ ኢትዮጵያን ክፍል የበቀል መወጫ እያደረገው ነው”፤ ነዋሪዎች

ላይቆም የተቀጣጠለው የሰሜን ምዕራብ ብረት አከል ህዝባዊ አመፅ የትግል ስልቱን እየቀያየረ ባህርዳር ደርሷል፡፡ አስር ወራትን ያስቆጠረው የነፃነት ኃይሎች እንቅስቃሴ ከገጠር ሽምቅ ውጊያ ወደ ከተማ የደፈጣ ቦምብ ጥቃት ተሻግሯል፡፡ በሁለት ወር ጊዜ ውስጥ ዘጠኝ የቦምብ ፍንዳታ ደርሷል፡፡ ድርጊቱ ሰላም የነሳው ህወሃት “የአማራ ክልልን የበቀል መወጫ እያደረገው” መሆኑ ይነገራል፡፡

ህወሓት/ኢህአዴግ ሙሉ የደህንነት አቅሙንና የበዛ የመከላከያ ኃይሉን አማራ ክልል ላይ ቢያደርግም የነፃነት ኃይሎች ተከታታይነት ያለው ጥቃት ከመፈፀም ያገዳቸው ኃይል የሌለ መሆኑ እየታየ ነው፡፡ የመጀመሪያዉ ዙር የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከመጠናቀቁ ከአንድ ወር በፊት መጋቢት የመጀመሪያ ሳምንት እስከ ሁለተኛዉ ዙር አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የመጀመሪያ ወር ሚያዚያ አራተኛ ሳምንት ድረስ ጎንደር ከተማ ውስጥ ሰባት፤ ባህርዳር ከተማ ሁለት በድምሩ ዘጠኝ የቦምብ ፍንዳታዎች ደርሰዋል፡፡

የቦምብ ጥቃቶቹ ያነጣጠሩት በአገዛዙ ማህበራዊ መሰረቶች (ባለስልጣናቱ በእጅ አዙር የሚነግዱባቸው ሆቴሎች፣ የደህንነቱ አባሪ ተባባሪ የሆኑ ስውር ነጭ ለባሾችን ቤት፣ የአገዛዙ ተሽከርካሪዎች፣ . . .) ላይ መሆኑ ደግሞ የነፃነት ኃይሎችን መዋቅራዊ ጥንካሬ አጉልቶ ያሳየ ተብሎለታል፡፡ በሁለት ወር ውስጥ ብቻ ዘጠኝ የቦምብ ጥቃት ባስተናገዱት ሁለቱ ከተሞች የወጣቶች የጅምላ እስር ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ ከሁለቱም ከተሞች የሰበሰብናቸው መረጃዎች እንደሚያመለክቱት “ህወሓት ክልሉን የቂም በቀል መወጫ እያደረገው ይገኛል” ሲሉ ነዋሪዎች ህወሓትን ይወነጅላሉ፡፡ “ከእያንዳንዱ የቦምብ ጥቃት በኋላ ፍንዳታው የደረሰበት ከተማ በተኩስ እሩምታ ሲታመስ ያድራል” የሚሉት ነዋሪዎች “በሌሊት ወጣቶችን ከመኖሪያ ቤታቸው አፍሶ መውሰድ የተለመደ ድርጊት ሆኗል” ይላሉ፡፡

በአንፃሩ በየጊዜው እየደረሱ ባሉ የቦምብ ጥቃቶች የአገዛዙ ልሳን በሆኑ የሚዲያ ውጤቶች መግለጫዎች ሲሰጡ ባይሰማም ከጉዳዩ አሳሳቢነት የተነሳ የአሜሪካ መንግሥት አዲስ አበባ ባለው ኤምባሲው በኩል ዜጎቹ ወደ ባህርዳርና ጎንደር እንዳይጓዙ በይፋ ክልከላ ማድረጉን አሳውቋል፡፡ በየጊዜው እየደረሱ ባሉ የቦምብ ፍንዳታዎችና የሽምቅ ውጊያዎች የተነሳ በሰሜን ምዕራብ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ቁሟል፡፡ ለዕለት ፍጆታነት ከሚውሉ ሸቀጣሸቀጦች ውጪ ይህ ነው የሚባል የንግድ እንቅስቃሴ አለመኖሩ ደግሞ አካባቢው በኢኮኖሚ እንዲደቅ አድርጎታል፡፡

በቀደመው አመፅ የፈራረሰበትን መዋቅር በድህረ-“ተሃድሶ” እንቅስቃሴው መልሶ ማቋቋም የተሳነው ብአዴን የመካከለኛ አመራሩ ሽሽት መቆሚያ አጥቷል፡፡ የሰሜን ምዕራብ የመረጃ ምንጮቻችን ከእያንዳንዱ የቦምብ ጥቃት ጀርባ መዋቅራዊ ሽፋን እንዳለዉ ይጠቁማሉ፡፡

“በርግጥም በእስካሁኑ የቦምብ ጥቃቶች ተጠያቂ የተደረገ አካል አለመኖሩ የነፃነት ኃይሎች መዋቅራዊ ድጋፍ እንዳላቸው አስረጅ ምሳሌ ሆኖ ሊቀርብ ይችላል” የሚሉ አስተያየት ሰጪዎች አሉ፡፡ ጎንደር ውስጥ በሁለት ወራት ከደረሱት የቦምብ ጥቃቶች ውስጥ አምስቱ ጥቃቶች በኤፍ ዋን (F one) ቦምብ የተፈፀሙ ሲሆን፤ በተመሳሳይ መልኩ ከሦስት ቀን በፊት ባህርዳር ከተማ ውስጥ በሙዚቃ ድግስ ላይ የደረሰው የቦምብ ጥቃት በፍንዳታና በማፈንጠር አቅሙ አቻ የሌለው እስራኤል ሰራሹ ኤፍ ዋን (F one) ቦምብ መሆኑን የመረጃ ምንጮቻችን ዘገባ ያመለክታል፡፡

ዳሽን ቢራ ከገበያ ድርቀት እስከ ቦምብ ጥቃት!

ከህዝባዊ አመፁ መቀስቀስ ጋር ተያይዞ ዳሽን ቢራ ክፉኛ በገበያ ድርቅ መመታቱ ይታወቃል፡፡ ዳሽን ቢራ ፋብሪካ ከገጠመው የገበያ ድርቀት ለማገገም “ባለ አገሩ” በሚል የቢራ ዓይነት (ብራንድ) ገበያውን ተቀላቅሏል፡፡ አዲሱን ቢራ ለማስተዋወቅ ያለመ የሙዚቃ ድግስ በባህርዳር ከተማ ለማዘጋጀት ደፋ ቀና ሲሉ የከረሙት የፋብሪካው ከፍተኛ አመራሮች፤ በነፃነት ኃይሎች የቦምብ ጥቃት የሙዚቃ ድግሱ ተቋርጧል፡፡

እንደ ጎልጉል የአካባቢው የመረጃ ምንጮች ዳግማዊ ትንሳኤ ላይ ሊካሄድ የታሰበው ይሄው የሙዚቃ ድግስ በአርቲስቶች የፕሮግራም መጣበብ ወደ ሚያዚያ 21/2009 ዓ.ም. ሊሸጋገር ችሏል፡፡ “ክብር ለባላገሩ” በሚለው የሙዚቃ ድግስ አርቲስት ማዲንጎ አፈወርቅ እንዲገኝ ተጋብዞ የነበረ ቢሆንም አርቲስቱ “ከህዝብ ጋር መቀያየም አልፈልግም!” በሚል ፍቃደኛ ሊሆን እንዳልቻለ የመረጃ ምንጮቻችን ዘገባ ያመለክታል፡፡

በዕለቱ የሙዚቃ ድግስ ተገኝተው የሙዚቃ ሥራዎቻቸውን ለመጫወት ከተስማሙት ታዋቂ አርቲስቶች ውስጥ ሙሐሙድ አህመድ፣ ኩኩ ሰብስቤና አረጋኽኝ ወራሽ ይገኙበታል፡፡ በማህበራዊ ድረ-ገፆች ይህን የሙዚቃ ድግስ በተመለከተ ሊካሄድ እንደማይገባ የሚያስጠነቅቁ ማስጠንቀቂያዎች በተደጋጋሚ ሲስተጋቡ እንደነበር ይታወሳል፡፡ አርቲስት ሙሐሙድ አህመድ የተቃውሞውን መካረር ታዝቦ አርብ መጋቢት 20/2009 ዓ.ም. ለኮንሰርቱ አዘጋጆች በሙዚቃ ድግሱ ላይ እንደማይገኝ ማሳወቁን የባህርዳር ምንጮቻችን ይጠቁማሉ፡፡

በተመሳሳይ መልኩ አርቲስት አረጋኽኝ ወራሽ ቅዳሜ ሚያዚያ 21/2009 ዓ.ም. በጥዋት 1፡00 ሰዓት የአውሮፕላን በረራ ወደ ባህርዳር የተጓዘ ቢሆንም የብአዴኑ የሙዚቃ ድግስ ህዝባዊ ተቀባይነት የራቀው የከፍተኛ አመራሩ ተፅዕኖ መሆኑን ሲረዳ በሙዚቃ ድግሱ ላይ መገኘት እንደማይችል አሳውቆ በ7፡00 ሰዓቱ የአውሮፕላን በረራ ወደ አዲስ አበባ ተመልሷል፡፡ ይህን መረጃ በተመለከተ የባላገሩ ፕሮዳክሽን ባለቤት አርቲስት አብርሃም ወልዴ ከ “ባለ አገሩ ቢራ” ጋር የተያያዘ የኪነ ጥበብ ሥራ እንዳልሰራና ፕሮዳክሽኑ ምንም አይነት የሥራ ግንኙነት እንደሌለው በይፋዊ የፌስቡክ ገፁ ባሳወቀበት መረጃ የአርቲስት አረጋኽኝ ወራሽን ጉዳይም አሳውቋል፡፡

በአንፃሩ አርቲስት ኩኩ ሰብስቤ በሙዚቃ ድግሱ ላይ ለመጫወት በመወሰኗ ዕለተ ቅዳሜ ሚያዚያ 21/2009 ዓ.ም. በባህርዳር ከተማ የወጣቶች ማዕከል አዳራሽ ምሽት 1፡00 ሰዓት ላይ መካሄድ በጀመረው የሙዚቃ ድግስ ተገኝታ ነበር፡፡

“ክብር ለባለ አገሩ” የሚለውን የሙዚቃ ድግስ በተመለከተ የሚኮንኑና የሙዚቃ ድግሱ እንዳይካሄድ የሚያስጠነቅቁ ጥብቅ መግለጫዎች በማህበራዊ ድረ ገፆች ሲተላለፍ የነበረ በመሆኑ የቅዳሜው የሙዚቃ ድግስ በታጠቁ ኃይሎች፣ በዳሽን ቢራ የሽያጭና ማስታወቂያ ሰራተኞች እና በካድሬዎች የተሞላ ነበር የሚሉን የባህርዳር ምንጮቻችን “ኩኩ ሰብስቤ ወደ መድረክ ወጥታ ‹ቻልኩበት› የሚለውን የሙዚቃ ሥራዋን እያቀረበች በነበረበት ቅፅበት ከተለያየ አቅጣጫ ሁለት የቦምብ ጥቃቶች ተፈፀሙ” ይላሉ፡፡ እንደ መረጃ ምንጮቻችን ዘገባ በጥቃቱ ሁለት የፌዴራል ፖሊስ አባላት ሲገደሉ፣ 13 በጽኑ ቆስለዋል፡፡ 31 የሚሆኑ ሲቪልና የታጠቁ ኃይሎች ቀላል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡

ከቦምብ ጥቃቱ በኋላ አርቲስት ኩኩ ሰብስቤ ወደ ፈለገ-ህይወት ሆስፒታል ተወስዳ ህክምና የተደረገላት መሆኑን የመረጃ አቀባዮቻችን ጠቁመዋል፡፡ አርቲስቷ በድንጋጤ ራሷን ከመሳቷ ውጪ ይህ ነው የሚባል ጉዳት አልደረሰባትም፡፡ ከዚሁ የቦምብ ጥቃት ጋር ተያይዞ ባህርዳር ከተማ ቅዳሜ ለእሁድ አጥቢያ በተኩስ እሩምታ ስትታመስ ማደሯን ከወደ ባህርዳር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ ይህ ሪፖርት እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ በከተማዋ የጅምላ እስር ተጠናክሮ እንደቀጠለ ነው፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የአገዛዙ ማህበራዊ መሰረት የነበሩት አርቲስቶች በህዝባዊ ጫና ከአገዛዙ ጋር የነበራቸውን መሞዳሞድ እያቆሙ ይገኛሉ፡፡ አገዛዙ በሚያዘጋጃቸው የሙዚቃ ድግሶች መታደም ከህዝብ ጋር በቀጥታ መላተም መሆኑ እየገባቸው የመጣ በመሆኑ የሚቀርብላቸውን ግብዣ ሲገፉ እየታየ ነው፡፡ ለዚህ ምሳሌ መሆን የሚችሉት አርቲስት መሐሙድ አህመድ፣ ማዲንጎ አፈወርቅና አረጋኽኝ ወራሽ፣ . . . ተጠቃሽ ናቸው፡፡ አንዳንድ አድርባይ አርቲስቶች የህዝብን የተቃውሞ ድምፅ አለመስማት የሚያስከትለውን መዐት ዛሬም ድረስ ከከባድ ድንጋጤዋ ያላገገመችውን አርቲስት ኩኩ ሰብስቤን ጠይቆ መረዳት ይችላሉ ሲሉ አስተያየታቸዉን የሰጡን የባህርዳር የመረጃ ምንጮቻችን፤ የነጻነት ኃይሎች ጥቃት “ትግሉ አይቆምም” የሚል መልዕክት እንዳለዉ ይጠቁማሉ፡፡ ከዚሁ ጋር አያይዘዉ በባህርዳሩ የሙዚቃ ድግስ ላይ የደረሰው የቦምብ ጥቃት ባልደረቀ የንፁሃን ደም ላይ ቁሞ መዝፈን ለሚያስደስታቸው ለሌሎች አርቲስቶች ጥሩ ትምህርት ነው ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡ “ከሁሉ በላይ የባህርዳሩ የቦምብ ጥቃት የነፃነት ኃይሎች ጥቃት ከዳር ወደ መሀል የመሻገሩ ብስራት ተደርጎ ሊታይ ይችላል” በማለት ለጎልጉል አስተያየታቸውን የሰጡ “አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ሰሜን ምዕራብና አካባቢው የቦምብ ቀለበት መፍታት ሽንኩርት የመላጥ ያህል ቀሏል” ሲሉ እየታየ ያለዉን ተጋድሎ በተመለከተ አስተያየታቸዉን ሰጥተዋል፡፡

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በተከታታይ እንዳቀረባቸዉ የአካባቢዉ ዘገባዎችና አሁን በተጨባጭ በአገዛዙ ላይ እየደረሱ ካሉ ጥቃቶች አኳያ በጊዜ ሂደት የአገዛዙ ማህበራዊ መሰረቶች እየተሸረሸሩ የነፃነት ኃይሎች መዋቅራዊ ድጋፍ እየጠነከረ መምጣቱን መመስከር ይቻላል፡፡

እስካሁን በተካሄዱት ጥቃቶች በይፋ ኃላፊነት የወሰዱ ባይኖሩም ካካባቢዎቹ የሰበሰብነው መረጃ እንደሚያመላክተው እንደ ብረት አልባው ሕዝባዊ ተቃውሞ ይህኛውም ሕዝባዊነት ያለውና በህወሃት/ኢህአዴግ አገዛዝ የተማረሩ የሚወስዱት ርምጃ እንደሆነ ለመረዳት ችለናል፡፡ (የመግቢያው ፎቶው ለማሳያ የቀረበ ሲሆን የተገኘው እዚህ ላይ ነው)


EmbassyMedia - ራብዓይ ግንባር!

Dehai Events