Dehai News

Goolgule.com: የሚንተከተከው የአፍሪካ ቀንድ አካባቢና አንድምታዎቹ!

Posted by: Berhane Habtemariam

Date: Monday, 29 May 2017

የሚንተከተከው የአፍሪካ ቀንድ አካባቢና አንድምታዎቹ!

 
  • ጋምቤላ እና ብዙ ዋጋ የተከፈለበት ኦጋዴን አደጋ ላይ ናቸው!
  • ኦጋዴን ተገንጥሎ ወደ ሞቃዲሾ እንዲጠቃለል መለስ ዜናዊ ፈርሟል። የሰነዱ ግልባጭ እንግሊዞች እጅ አለ።

ወያኔ በሶስት አቅጣጫ እንደ ቆዳ የተወጠረ ቡድን ነው ሲባል

፩ ለዘመናት ሲተዳደርበት የኖረው ኢህአዴግ በሚለው ማእቀፍ ውስጥ የነበረው የአሽከርና የሎሌ ግንኙነት ማብቃቱና በራሱ በህወሃት መካከል ያለው የሃይል ክፍፍል ያመጣው አጠቃላይ የስርአቱ አደጋ መሆኑ፣

፪ ለረጅም ግዜ ሞቅ ቀዝቀዝ ሲል የነበረው ህዝባዊ ተቃውሞ መልኩን ቀሮ ወደ ማይመለስ ህዝባዊ ተጋድሎ ማደጉና ከህዝባዊ ተጋድሎው ጀርባ ያሉት ነፍጥ ያነሱትን ድርጅቶች የመገዳደር ወይንም ችግሩን በፖለቲካዊ ውይይት ለመፍታት አቅም የማጣቱ ምክንያት ሲሆን

፫ኛው ክንፍ ደግሞ በምስራቅ አፍሪካ ላይ የተፈጠረው አለም አቀፍ የሃይል አሰላለፍ ላይ “በዚህ ሰፈር ያለኔ ማን አለ!” ሲል የነበረው የትግራዩ ገዥ ጉጅሌ በሂደት ትናንት የተፈጠረችው ደቡብ ሱዳን ሳይቀር መሳቂያና መሳለቂያ መሆኑ ብሎም ወያኔ ከማንኛው ጎን እንደሚቆም እና በየት በኩል ፍላጎቱን ማስፈጸም እንደሚችል እንኩዋን አቅጣጫውን የማመላከት አቅም ያለው ድንበር ዘለል የፖለቲካ መተንተኛ ማእከል የሌለው ነፈዝ መሆኑና እንዲሁም በሚሊሻ የሚመራ ቡድን የሩቁን ቀርቶ አፍንጫው ስር ያለውን እውነት እንኩዋን ለማየት አቅም የሌለው መሆኑን ያስረገጠ እውነት ነው።

ከላይ የጠቀስናቸው ሁለት ነባራዊ እውነታችዎች በየግዜው ብዙ የተባለባቸው በመሆናቸው ለዛሬው አካባቢያዊ ሁኔታዎች ላይ ብቻ በደምሳሳው ለማተኮር እሞክራለሁ።

ሰሜን ሱዳን

የጆርጅ ቡሽ አስተዳደር ሱዳንን ለአራት ለመክፈል የነበረው እቅድ በደቡብ ሱዳን ተጀምሮ ቀጣዩ ተረኛ ዳርፉር ላይ ሲደርስ ቀጥ እንዳለ ነው። የሴንትራል አፍሪካ መተራመስ እና ብዙ ደም የተገበረበት እና ሁለት ትውልድ ጨልጦ የጠጣው የደቡብ ሱዳን ነጻነት ወደ ሌላ ዙር ደም አፋሳሽ ሁኔታ ውስጥ መግባቱ የፈጠረው ትርምስ ቀጠናውን ሆደ ባሻ አድርጎታልና ቢያንስ አገሩ አሁን ባለበት ሁኔታ ተጨማሪ ቀዶ ጥገና እንደማይሸከም ፍንትው አድርጎ አሳቷል። በመሆኑም በአለማቀፍ የወንጀል ችሎት እንዲቀርብ ማደኛ ከወጣበት አልበሽር ጋር ከመጋረጃ ጀርባ (ጀንትል ማን አግሪመንት) በተደረገ አጣዳፊ ስምምነት ለግዜው እርሱ ወታደሩ ላይ ባለው ተጽእኖ እንዲሁም እስከ ታችኛው መዋቅር ድረስ የዘረጋውን ቤተሰባዊ ሰንሰለት አገሪቱን ጠርንፎ የያዘ በመሆኑም ጭምር ለግዜው ከእርሱ የተሻለ ጠንካራ ሃይል ማግኘት አይቻልም በሚል የማረጋጋቱን ድርሻ እንዲወጣ ከአሜሪካን አስተዳደር ቡራኬ ደርሶታል። በታህሳስ ወር ካይሮ ከሚገኘው መኖሪያ ቤቱ ወደ ካርቱም ያመራውና ግዜያዊ አስተዳደር እንዲመሰርት ግፊት እየተደረገበት ነው የተባለው አረጋዊው ሳዲቅ አልማህዲ ጉዳይ አሁን ባለው ሁኔታ የትም እንደማይደርስ ግልጽ ሁኗል።

ደቡብ ሱዳን

ከምእራብ አገር ጓዳ እያፈተለኩት የሚወጡት መረጃዎች እንደሚያሳዩት አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ደቡብ ሱዳን እንደ መንግስት ራንሷ ችላ በሁለት እግሯ በመቆም እንደ አገር መቀጠል የምትችልበት ሁኔታ ማብቃቱን ሙሉ ስምምነት የተደረበት በመሆኑ፤ ይኽ ኪሳራ ደግሞ እነርሱ በመጭዎቹ ዘመናት ሱዳንን በተመለከተ ያስቀመጡላት ወጥመድ ወጥቶ ሌላ አቅጣጫ የማስከተሉ ነገር የማይታበል በመሆኑ ይልቁንም የቻይና በሱዳን ውስጥ ለመዘርጋት የምታስበው የግንኙነት መስመር ሌላ የስጋት ምንጭ ጭምር እየሆነ በመምጣቱ ለሚቀጥለው አስር አመት ከአሜሪካ ከእንግሊዝና ከፈረንሳይ የተውጣጣ ግዜያዊ አስተዳደር ደቡብ ሱዳንን እንደሚረከባትና በሂደት የሊደርሽፕ ግንባታ እንደሚያኪያሂዱ እየተነገረ ነው። ከዚሁ ጋር በተያያዘ ግን የወያኔ ሚናና በጋምቤላ ውስጥ እየታፈኑ ካሉት ህጻናት ጀርባ ያለውን እንቆቅልሽ ሌላ ግዜ እመለስበታለሁ።

ሶማሊያ

ሶማሊያ ሲባል ከጎሳው በላይ አርቆ እንደ አገር ማሰብ የማይችል የዘላን አይነት ኑሮ የሰለጠነበት ህዝብ ነው። የኋላ ታሪኩም እንደሚያሳየው ከጎሳ አለቆች በላይ አገር የሚመስል ቅርጽ የያዘው በሶስት የአሮፓ አገሮች ቅርምት ውስጥ በገባ ሰሞን ብቻ ነው። በታሪክ አጋጣሚ አገር ተብሎ ፈረንሳይ፣ ጣሊያንና እንግሊዝ ለሶስት ተቀራምተው አስተዳረውታል። የኮሎኒያሊዝም ጸሃይ የጠለቀች ግዜ የፓን አፍሪካ ንቅናቄ የወለደውን የነጻነት አየር ምክንያት አድርጎ እንደ ማንኛውም አፍሪካ አገር ወረፋውን ጠብቆ አገር ነኝ፤ መንግስት አለኝ፤ ብሎ የራሱን ባንዲራ አቁሟል። ነገር ግን አገሩን እንዳገር ያስቆጠረው ዚያድ ባሬ የሚባል አንድ ሚሊሻ እንጅ ለሌ በጋራ ያስተሳሰራቸው የማህበረሰብ እሴት እንዳልነበረ አንዱ ማስረጃ የዚያድ ባሬን ከስልጣን መውረድ ተከትሎ አገሩ ሌሊቱን በፊሽካ ተበትኖ ማደሩ ሲሆን ከዛን ግዜ ወዲህ ሰሜን፣ ደቡብ እና ፑንትላንድ ተብለው እግር ወዳደረሳቸው ሄደዋል። ከአቅሙ በላይ በባላ-ሃይል እንደተወጠረ ላስቲክ ካባላው በተላቀቀ ግዜ ተመልሶ እንዲኮማተር የሶማሊያም ነገር እንዲሁ በዚያድ ባሬ ዘመን ተጀምሮ ከዚያድ ባሬ ጋር አብሮ ያከተመ ነው ብሎ መደምደም የማይቻል ነገር አይደለም።

ሰሜን ሶማሊያ

ሰሜን ሶማሊያ እንደ አገር እውቅና ባታገኝም ላለፉት ሩብ ምዕተ አመት አንጻራዊ በሆነ ሰላም የኖረችበት ዋናው ቁልፍ ነጥብ የሞቃዲሾው መንግስት እራሱን ችሎ እንደ መንግስት መቆም አለመቻሉ ነበር። ከሩብ ምዕተ ዓመት ወዲህ ባሳለፍነው ሁለት ወር ለመጀመሪያ ግዜ ቅርጽ ያለው መንግስት የሚመስል ነገር የሞቃዲሾው ሶማሊያ ውስጥ ተመሰረተ ሲባል ከማንም በላይ ስጋት ላይ የወደቀችው ሰሜን ሶማሊያ ናት። ምክንያቱም ግልጽ ነው፤ ይኽ በጉልበቱ ተንበረከከ የተባለው የሞቃዲሾ መንግስት ነገ በጥፍሩ ለመቆም እድል ካገኝ መጀመሪያ የሚበላው ሰሜን ሶማሊያን መሆኑ ግልጽ ሲሆን ሰሜኖችም በዚህ ጉዳይ ሲሰጉ ያለ አመክንዮ እንዲሁ ከባዶ ነገር ተነስተው አይደለም፤ ጥቂቶቹን እነሆኝ።

፩ የሰሜን ሶማሊያ እንደ መንግስት እውቅና ማግኘት አለመቻሉዋ ከአለማቀፉ ማህበረሰብ ማህበረሰብ የሉአላዊነት ዋስትና እንዳይኖራት ማድረጉ፤

፪ ከምዕራባውያንና የአረብ ኢምሬቶች መንግስታት በተጨማሪ ሶማሊያ በአሁኑ ሰአት የቱርክና የግብጽ የፍጥጫ (ፕሮክሲ ዋር) ሜዳ መሆኑውዋ፤

፫ ወያኔ እስካሁን ከሰሜን ሶማሊያ ጋር የነበረው ግንኙነት አልጋ ባልጋ የነበረ ቢመስልም አሁን ባለው አሰላለፍ ግን ፊቱን ወደ ሞቃዲሾው መንግስት መመለሱ ሌላው የሰሜን ሶማሊያ ስጋት ነው።

ለዚህም አዲሱ የሞቃዲሾ መንግስት አዲስ አበባ የሚገኘው የሰሜን ሶማሊያ ቆንሶላ ጽህፈት ቤት በአስቸኳይ እንዲዘጋና እስከዛሬ የነበረውን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ጭምር እንዲያቋርጥ የቀን ገደብ ሲያስቀምጥ ይህን የማያደርግ ከሆነ ሞቃዲሾ ላይ ለማን ቢሮ እንደሚሰጡ ቁልጭ አድርገው ነግረውታል.. ይኽ ማለት አዲሱ የፎርማጆ አስተዳደር ትንሽ ጉልበት እንዳገኘ ከተሰማው የመጀመሪያው አጀንዳ የሚሆነው ሰሜን ሶማሊያን መልሶ መያዝ መሆኑና የወያኔን እና የሰሜን ሶማሊያን ፍች አስቀድሞ ማስረገጥ መፈለጉ ከሚያወጣው መግለጫ የሚያስታውቅ ሲሆን ዛሬ የኦጋዴኑ ግንባር ከአርበኞች ግንቦት ሰባት ጋር እየፈጠረው ካለው ትብብር አንጻር ወያኔ ላይ ምርጫው የግድ ከሆነበት ወደ ሞቃዲሾ ማድላቱ የማይቀር መሆኑን ካሁን በፊት በሁለቱ ሱዳኖች መሃል ከወሰደው አቁዋም መረዳት ይቻላል።

በአንጻሩ ደግሞ ምዕራባውያን ጉልበት አጥፍተውበታል የሚበላው አዲሱ የሞቃዲሾ መንግስት ስልጣኑን በያዘ በጥቂት ሳምንታት ውስጥ አንድ ሚንስትር እና አንድ ቁልፍ ወታደራዊ ጀነራል ተገድሎበታል። ከዚህ ግድያ ጀርባ ከአልሸባብ ይልቅ የሰሜን ሶማሊያ ወይንም ለሰሜን ሶማሊያ ድጋፍ የሚያደርጉ አገሮች የስለላ ድርጅቶች እጅ እንደሚኖርበት መጠርጠሩ የሚያዋጣ ነው።

አሁን እየሆነ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ እንደሚያሳየው ብዙ የተደሰኮረለት የሶማሊያ ፕሬዝዳንት በማንኛውም ሰአት ሊገደል እንደሚችል የሚያመላክቱ በርካታ ምልክቶች አሉ። አንባቢያን ልብ ሊሉት የሚገባው ወሳኝ ነጥብ የሞቃዲሾ በተወሰነ ደረጃ ጠንክሮ መውጣት በተለይ ወያኔ አራት ኪሎ ባላበት ሁኔታ ለኛም ከሰሜን ሶማሊያ ባላነሰ አደጋ ያዘለ ነገር ሆኖ የመውጣቱን ነገር ሲሆን በሞቃዲሾ ትከሻ ላይ ተንጠላጥለው ኦጋዴንን ለመዋጥ ያሰፈሰፉትን እንግሊዝን የመሰሉ ኮብራዎች እንጥላቸውን የሚቆርጥ ዱብዳ ነው የሆነው።።

ኤርትራ

ኤርትራን የፈጠራት ሻዕቢያ ነው፤ ሻቢያን አጥፍቶ ኤርትራን እንደ አገር ማኖር አይቻልም። ለዚህም ነው ኤርትራውያን ምንም መንግስታቸው የሚከተለውን ፖሊሲ በመቃወም ወይንም ለተሻለ ኑሮ ስደትን እጣ ፋንታቸው ቢያደርጉም የዲያስፖራው ኢትዮጵያዊ በወያኔ ላይ የሚያደርገውን አይነት ዘመቻ ማድረግ ቀርቶ ሻዕቢያን በክፉ ማንሳት የማይፈልጉት። ለዚህም ነው ድንበር ተሻግረው ወደ ውስጥ የሚገቡትን ሰዎች ሰብስቦ ጸረ ሻቢያ ንቅናቄ ለመፍጠር ህልቁ መሳፍርት ጉድጓድ የቆፈረው ወያኔ በኪሳራ የወጣው።

ሻዕቢያ ወደ በረሃ የወረደው የቀዝቃዛው ጦርነት ፍጥጫ ጣራ በነካበት ወቅት ሲሆን በግዜው የቻይና እና የሶቪይት ኮሙኒዝም እንዳይስፋፋና የፓሲፊክን ባህረ ሰላጤ ሙሉ ለሙሉ በቁጥጥሩ ውስጥ እንዳያደርገው ለመታደግ ምእራባውያን በሲንጋፖር፣ በደቡብ ኮሪያና በታይዋን ያፈሰሱት ገንዘብ እነዚያን አገሮች በጥቂት አስርተ አመታት ውስጥ የተአምራዊ ምድር ሲያደርጋቸው ሻዕቢያ ከሳህል በረሃ ሆኖ አይቶታል። በመሆኑም እንደ ማንኛውም አገር የመፍጠር ህልም እንዳለው ቡድን ሻዕቢያም ይሕን “በምእራቡና በምስራቁ መካከል የነበረውን ፍጥጫ በመጠቀምና ቀይ ባህርን እንደ መጫወቻ ካርድ በመያዝ እነ ታይዋን የደረሳቸውን እጣ ፋንታ ኤርትራ ውስጥ በማምጣት አገራችንን ማሳደግ እንችላለን። ለዚህም ለተወሰነ አመትም ቢሆን በጣሊያን ስር እንደ አገር ተለይተን መኖራችን እርሾ ሆኖ ማገልገሉ እራሱን የቻለ ሃሴት ነው፤ በመሆኑም ኤርትራ በዚህ ስሌት ከሄደች የምስራቅ አፍሪካ ሲንጋፖር ትሆናለች” ሲል የነበረው መነሻው ይዅው ይመስለኛል።

አደገኛው ስሌት እና የሶስት አስርተ አመታቱ የበረሃ ትግል አደጋ ውስጥ የገባው ግን ሻቢያ አስመራ ሲደርስ ቀዝቃዛው ጦርነት ማብቃቱ ነው።አልተገናኝቶም ማለት ይኼው ነው። በመሆኑም ሻቢያና ወያኔ መንግስት ከሆኑ ቦሃላ ሻቢያ አዲሱን የአለም የሃይል አሰላልፍ በማየት ከኢትዮጵያ ጋር በምን አይነት ሁኔታ መኖር እንዳለበት እንደገና ከመጋረጃ ጀርባ ለመምከር አልሞከረም ማለት አይቻልም። መለስ እዚህ ላይ ምን ያህል ሻዕቢያን እንደገፋው ከግምት በላይ መሄድ የሚቻል ሲሆን ያ ባይሆን ዛሬ የኢትዮጵያና የኤርትራ ፖለቲካ ሌላ መልክ ሌላ ይዘት ይኖረው እንደነበር ለማወቅ ከሳሞራ የኑስ አቅም ትንሽ ከፍ ያለ ግንዛቤ ብቻ በቂ ነበር። የትግራይን እረኞች ሰብስቦ ፣ መንግስቱ ሃይለማርያም እንዳለው “ወያኔን ሱሪ አስታጥቆ” እና በአንቀልባ አዝሎ ሚኒሊክ ቤተመንግስት ያስገባው ሻቢያ ትንሽ አገር ይዞ ሲቀር ወያኔ ደግሞ ኢትዮጵያን የምታክል አገር ይዞ የአካባቢው ሃይል “እኔ ነኝ” ቢልም ቅሉ እውነታው ግን ከመሃል አገሩ ደጀን ውጭ ወያኔ ማለት ለሻቢያ ምን ማለት እንደሆነ ግልጥ ነው። ወያኔ በድኩማን አምላኪዎቹና እና በውጭ መንግስታት ፊት እራሱን እንደ ዳልጋ አንበሳ አስመስሎ ሲያቀርብ የኖረውን ያህል በሻቢያ በኩል ሲሆን ግን ዳልጋ ድመት መሆኑን አንዱ መገለጫ እርቅ ፍለጋ ሰባ ሁለት ግዜ ያህል ሽማግሌ መላኩም ነው።

ዛሬ ሌላ ቀን ነው። ባለፈው ሁለት አስርተ አመታት የነበረው የግሎባላይዜሽን ዘመን ለወያኔ አልጋ ባልጋ የነበረውን ያህል ድህረ አረብ እስፕሪንግ እየተፈጠረ ያለው የጅኦ ፖለቲካ ቀውስ ግን ምን ይዞበት እንደመጣ ወያኔ ባይኑ ብሌን ቁጭ ብሎ እያየው ነው። የቀይ ባህርም ጉዳይ መለስ የተባለ ድንቁርና እና የበታችነት በሽታ ተጋግዘው ያቆሙት እኩይ ሊያጣጥለው እንደሞከረው “ወደብ ማለት ማንም ገንዘብ ካለው ሊገዛው የሚችለው ሸቀጥ ነው። ሻቢያ ከፈለገ ግመሉን ያጠጣበት” ብሎ እንደተሳለቀበት እንዳልሆነም;ባህር በር ማለትም ከወደብነት ባሻገር ከህልውናችን ጋር ያለውን ቀጥተኛ ግንኙነት ለማወቅ ዛሬ ስንት አገሮች በቀይ ባህር ዙሪያ ሮኬቶቻቸውን እንዳጠመዱ ማየት ነው። በዚህ ስሌት አንጻር ሲታይ የወያኔ መንግስት ማለት የዛሬ ሶስት ሽህ አመት ከነበሩትና የቀይ ባህርን አስከብረውት ከነበሩት ጥንታዊ ነገስታቶቻችን ጋር ሲነጻጸር ምን ያህል ራዕይ አልባና በመንፈስም የጨነገፈ እንደ ነበር ያሳያል።

የወያኔ ድንፋታ እና ሻቢያን በተመለከተ አዲስ ፖሊሲ ቀርጫለሁ ስለ ማለቱ ዛሬም እንደትናቱ የሻቢያ ግምገማ እንደሚያሳየው ወያኔ ለተራ የፖለቲካ ፍጆታ ሲባል ባለፈው አመት እንዳደረገው ድንበር አካባቢ በጣም መለስተኛ የሆነ ትንኮሳ ከማድረግ ባለፈ ወደ ሙሉ ወረራ የሚሄድ ምንም አይነት ወታደራዊ፣ ስንልቦናዊ ወይንም ፖለቲካዊ ጥንካሬ እንደሌለው ነው።

የወያኔ የፖለቲካ ኪሳራ ሁላችንም የምናውቀው ሲሆን ወታደራዊ አቅሙን በተመለከተ የተወሰኑ ምስሌዎችን ጠቅሰን ማለፍ እንችላለን።

፩ ባለፈው አመት ወያኔ አለኝ የሚለው የሄሊኮፕተር አብራሪ አንዱን ዘመናዊ የጦር ሄሊኮፕተር ለልምምድ ይዞት ሲነሳ ወዲያውኑ መሬት ላይ ከነበሩ ሌሎች ሶስት ሄሊኮፕተሮች ጋር በመከስክለሱ የተነሳ በአንድ ግዜ አራቱም ዘመናዊ ሄሊኮፕተሮች ሙሉ ለሙሉ ተቃጥለዋል። ይህ እንግዲህ ወደ ጎረቤት ኤርትራ ከኮበለሉት ሄሊኮፕተርፕተሮች በተጨማሪ መሆኑ ነው።

፪ ወያኔ አሁን ያሉት ሄሊኮፕተሮች አምስት ብቻ ሲሆን እነሲም ቢሆን አንጻራዊ በሆነ መልኩ አገልግሎት የሚሰጡት ሜዳማ በሆኑ የጅጅጋና ኦጋዴን አካባቢ በመሆኑ በጣም ተራራማ ለሆነው የሰሜን ኢትዮጵያ የውጊያ ቀጠና ምንም አይነት ጥቅም ሊሰጡ የሚችሉበት ሁኔታ እንደሌለ የታወቀ የተረዳ ነገር ነው።

፫ ተዋጊ ጀቶችን በተመለከተ ወያኔ ያሉት አብራሪዎች ዩክሬንን ከመሰሉ የምስራቅ አውሮፓ አገሮች የተገዙ ቅጥረኛ ነፍሰ ገዳዮች (መርሰነሪ) መሆናቸው፤ እና አንድ በሶስተኛ አገር ውስጥ የበረራ አገልግሎት ለመስጠት የሚቀጠር የውጭ አገር ዜጋ የበረራ አገልግሎቱን መስጠት የሚችለው በኢትዮጵያ ክልል ውስጥ ብቻ መሆን እንዳለበት አለም አቀፍ ህግ የሚያስገዽድ በመሆኑ ወያኔ ከሻቢያ ጋር ጦርነት ቢገጥም ወደ ኤርትራ ክልል ገብቶ መደብደብ የማይችል መሆኑ የአየር ሃይሉን አገልግሎት ጥቅም አልባ አድርጎታል።

፬ እግረኛውን በተመለከተ ወያኔ አንድም ለፕሮፓጋንዳ ሽፋን ይኽን ያህል ሃይል አለው እንዲባል አንድም በሌሉ ወታደሮች ሽፋን ለደመወዝ ተብሎ ከሚመደብ በጀት የጀነራሎችን ባንክ ለማጣበብ ሲባል ወያኔ ከሁለት መቶ ሽህ በላይ መደበኛ ወታደር አለኝ ይበል እንጅ እውነታው ግን ከነግሳንግሱ እና ወጥ ቤት ሰራተኛውን ጨምሮ ብዛቱ ከአንድ መቶ ሃያ ሽህ እንደማይበልጥ ሊሰመርበት ይገባል። በዚያ ላይ በዘር የተከፋፈለ፣ ላለፉት ሰባት አመት እረፍት ወጥቶ የማያውቅና ከተራው የኢትዮጵያ ህዝብ በላይ የወያኔ ዘረኛ ፖሊሲ ሰለባ በመሆኑ እርሱም እንደማንኛውም ተራ ዜጋ አጋጣሚውን የሚጠብቅ ነው።

በመሆኑም ከላይ ያሉትን ጥቂት ምክንያቶች እንኳን በደምሳሳው ሲታዩ የወያኔ ፉከራ ምን ያህል ባዶ በርሚል እንደሆነ ግልጥ ነው።

ኦጋዴን እና የምዕራብ መንግሥታት ተጽእኖ

ለምሳሌ ኦጋዴን በተመለከተ የምዕራብ አገሮች ፍላጎት ሶስት አይነት መልክ ያለው ሲሆን

* ኦጋዴን ተገንጥሎ ወደ ሞቃዲሾ እንዲቀላልቀል እየሰሩ ያሉ አገሮች አሉ – በመርህ ደረጃ ምን ማለት እንደሆነ ግልጽ ባይሆንም ኦጋዴን ተገንጥሎ ነገር ግን እራሱን ችሎ እንዲኖር የሚፈልጉ አሉ፤ እንዲሁም ኦጋዴን በኢትይጵያ ስር ሆኖ መቆየቱ አማራጭ የለውም ብለው በግልጽም በስውርም የሚደግፉ መንግስታትም አሉ።

* ኦጋዴንን ለመገንጠል የተወሰነ የመንገድ እርቀት የሄዱ አሉ ስንል፤ ገና በህይወት እያለ መለስ ዜናዊ ለኦጋዴን መገንጠል እውቅና እንዲሰጥ አብራ ስታሴር የከረመችውን ተንከሲስ አገር ማን እንደምትሆን የሚጠፋው አለ ማለት አይቻልም። ይሕች አገር እረዘም ላለ ግዜ ግዜ ወስዳ በአመዛኙ ዳውሮ የሚባለው; በኦጋዴን የሚኖረውና ዚያድ ባሬ ከሚወልድበት ጎሳ የሚመዘዝ የዘር ግንድ ያለውን ፎርማጆን ከሰባት አመት የማዋቀር ሂደት ቦሃላ ከምእራብ አገር መልሰው በሞቃዲሾ ላይ ያነገሱት በዋናነት የኦጋዴንንም ጉዳይ ጭምር ታሳቢ በማድረግ መሆኑን ሊታወቅ ይገባል።

የአርበኞች ግንቦት ሰባት እና የኦጋዴን ብሔራዊ ግንባር

ወያኔ እግሩን በዚህች አገር ላይ ከተከለበት ቀን አንድ ጀምሮ ሲከተለው የኖረው አገር የማፍረስ ሂደት በዋናነት ያጠነጠነው መሃሉን በማዳከምና ጽንፈኛ የሆኑትን በማጠናከር ብሎም ወደ ውጭ በመግፋትና ከኢትዮጵያዊነት እትብት በመበጠስ ነው። ለዚህም እንድ ኦጋዴን ብሄራዊ ነጻ አውጭ ግንባር አይነቶቹ ቡድኖች ተጠቃሾች ናቸው። ላለፈው ሩብ ምእተ አመት ጎሰኝነት ህገመንግስታዊ ቡራኬ አግኝቶ ክፉኛ የተራገበባት አገራችን ዛሬ አዲስ አበባ ላይ አለሁ የሚለው የሃይለ ማርያም ካቢኔት የማይቆጣጠራቸው ወይንም የማይቆጣቸው ትናንሽ መሳፍንት በብሄር ብሄረሰቦች እራስን በማስተዳደር ስም እራሳቸውን እንደ መንግስት መቁጠራቸው የተለመደ ነገር ሆኗል። ነገሩ በሂደት አዋጭ ነው ወይንስ አይደለም የሚለውን ትተን አሁን ባለንበት ነባራዊ ሁኔታ ኦጋዴንንም ሆነ የጋምቤላን ክልል እንዳይገነጠሉ የሚያግዳቸው ምንም አይነት ውስጣዊ ምክንያት እንደሌለ ኢትዮጵያውያን በግልጽ ማወቅ አለብን።

ዛሬ ግዜው ይዞት የመጣውና ለምዕመናን መገለጥ የጀመረው አንድ እውነት ማዕከላዊ መንግስት ነኝ የሚለው አካል እንደ አሮጌ ዘምቢል ወላልቆ ክልሎቹን መቆጣት የማይችልበት ደረጃ የመውረዱን ያህል በተጻራሪው ደግሞ መሬት ላይ ወርደው ነፍጥ ባነሱት ጸረ ወያኔ ንቅናቄውች በኩል ከጎሰኛዎቹ ይልቅ ብሔራዊ አጀንዳ ያለቸው ድርጅቶች ይበልጥ ጎልተው በመውጣታቸው እንደ ኦጋዴን ብሄራዊ ነጻ አውጭ ግንባር የመሰሉ ጽንፈኛ ቡድኖች ግማሽ መንገድ ድረስ መጥተው ከአርበኞች ግንቦት ሰባት ጋር ለመስራት መወሰናቸው እንደ አንድ አገር ቀላል የማይባል ስኬት መሆኑን ነው።

ጥያቄው “እንግሊዝና ወያኔ ኦጋዴንን ገንጥለው ከሞቃዲሾ ጋር ለማዋኸድ ላይ ታች በሚሉበት በዚህ አጣብቂኝ ወቅት የኦጋዴን ብሄራዊ ንቅናቄ ፊቱን ወደ ማእከላዊው ፖለቲካ የመለሰበት ውጫዊ (አካባቢያዊ) ምክንያት ምንድን ነው?” ለሚለው ቁልፍ ነጥብ ጥቂት የሚባሉትን ምክንያቶቹን እዚህ ላይ መጥቀሱ ተገቢ ነው።

፩ ዛሬም ሆነ ነገ በሶማሊያ ዙሪያ ሊነሳ የሚችለው የጅኦ ፖለቲካ የሃይል አሰላለፍ ሲታይ በጣም በርካታ አገሮች እያኮበኮቡበት የመሆኑን ነገር ለሚያስተውል ሰው የነገዋ ሶማሊያ የዛሬዋን ሶሪያ የማትሆንበት ምንም አይነት ዋስትና አለመኖሩን ዛሬ ከዘገየም ቦሃላም ቢሆን ማስተዋሉ..

፪ ለኢትዮጵያ መዳከም ትልቁን ድርሻ የሚጫወተው ወያኔ አገሪቱን አዳክምበታለሁ ብሎ በዘረጋው የዘር ፖለቲካ የተነሳ እየተፈጠረ ያለው የብሄርተኝነት ስሜት የተነሳ ማን የመጀመሪያ ሰለባ ሊሆን እንደሚችል ግልጽ ሆኖ መውጣቱ፤ በዚህም ወያኔ አገሪቱን ገድሎ ከመጨረሱ በፊት ያጠመደው ፈንጅ እጁ ላይ መፈንዳቱ እና ዛሬ ከሰሜን ጎንደር የተነሳው ጸረ ወያኔ እምቅ ሃይል አሁን ባለው አካሄድ ነገ ሸዋ ሲደርስ እራሱን የኦጋዴን ጽንፈኛ ቡድን ቀርቶ ማንንም በቀናት ውስጥ የመጨፍለቅ (potential danger) አቅም ከባድ እንደሚሆንና እንዲህ ዝም ብሎ በቀላሉ እንደማይባረድ ቀድሞ የመረዳቱ ነገር ካሁን የአርበኞች ግንቦት ሰባትን እንደ ስትራቴጂካል አጋር እንዲያየው ግድ ብሎታል።

ምንም ይሁን ምንም ከገባንበት የጎሰኝነት ስሜት ባሻገር ለነገይቱ አገራችን ህልው መሆን ካሰብን እንዲህ ያሉ ግንኙነቶች የአካባቢውን የሃይልም ሚዛን በማዛነፍ እረገድ የሚጫወቱት ሚና ቀላል አለመሆኑ ብቻ ሳይሆን የወያኔን ውድቀት በማፋጠኑና ሴንትራል ፖለቲካውን ለማጠናከር የሚኖራቸው ሚና ጉልህ ነው።

የአርበኞች ግንቦት ሰባት ከረጅም ግዜ እልህ አስጨራሽ ድርድር በኋላ ይህን ጽንፈኛ ቡድን አሳምኖ ወደዚህ ደረጃ ማምጣቱ የሚበረታታ ተግባር ሲሆን ይኽ ጅምር ወደ ፍሬ ክብር እንዲደርስ በላይኛው አመራር ላይ የተጀመረው መተባበር እስከታች ድረስ በመውረድና በመቀናጀት ነገ ደግሞ ከፖለቲካ ትብብርም ባሻገር ወደ አንድ የጋራ ወታደራዊ ኮማንድ ስር የሚጠቃለልበትን አካሄድ ከወዲሁ መጀመር የሚጠበቅበት ሲሆን በቀጣይም ሌሎችም አገራዊ አጀንዳ ያላቸው ድርጅቶች ሁሉ ይሕንን አር አያነት ያለው ትብብር ቢከተሉ የወያኔን እድሜ በማሳጠር አገሪቱን የመታደጉን እርብርብ ቀላል ያደርጉታል።

መስቀሉ አየለ እንድናትምላቸው በፌስቡክ የላኩልን (meskeluayele@gmail.com)


6ይ ክፋል: ማዕበል ስርሒት ፈንቅል - የካቲት 1990 - ሰነዳዊት ፊልም| sirihit fenkil 1990 - part 6 - ERi-TV Documentary

Dehai Events