አዲስ አበባ ፣ ሃምሌ 9 ፣ 2018 (ኤፍ ቢ ሲ) ኢትዮጵያ የመንግስታቱ ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት በኤርትራ የጣለውን ማዕቀብ እንዲያነሳ ይፋዊ ጥያቄ አቀረበች።
የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በኤርትራ ያደረጉትን ይፋዊ ጉብኝት አጠናቀው አዲስ አበባ ገብተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ አዲስ አበባ ከተመለሱ በኋላ ከመንግስታቱ ድርጅት ዋና ፀሃፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ ጋር ተወያይተዋል።
በዚህ ወቅትም ተመድ በኤርትራ የጣለውን ማዕቀብ እንዲያነሳ ለዋና ፀሃፊው ይፋዊ ጥያቄያቸውን አቅርበዋል።
ጥያቄው የቀረበላቸው የመንግስታቱ ድርጅት ዋና ፀሃፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ በበኩላቸው፥ ኤርትራ ላይ የተጣለው ማዕቀብ ከዚህ በኋላ ብዙ ጊዜ ተግባር ላይ እንደማይቆይ ተናግረዋል።
ዋና ፀሃፊው ኢትዮጵያና ኤርትራ መደበኛ ግንኙነታቸውን ለመጀመር መስማታቸውን ተከትሎ፥ ምክር ቤቱ በኤርትራ ላይ የጣለው ማዕቀብ ከዚህ በኋላ ተግባር ላይ የሚቆይበት ምክንያት የለም ብለዋል።
ከዚህ ባለፈም ዋና ፀሃፊው ሁለቱ ሃገራት ከድንበር ጋር በተያያዘ የደረሱት የድንበር ማካለል ጉዳይ እንዲሳካም ተመድ ሁኔታዎችን ለማመቻቸት ዝግጁ መሆኑንም ገልጸዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በኤርትራ በነበራቸው ቆይታ ከፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ጋር የተለያዩ ስምምነቶችን ተፈራርመዋል።