Date: Monday, 04 May 2020
አዲስ አበባ ፣ (ኤፍ ቢ ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ከኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ጋር በመሆን የባቱ ዱግዳ የመስኖ ልማት ፕሮጀክትን መርቀዋል።
በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ እንዲሁም የቀድሞው የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ተገኝተዋል።
የመስኖ ፕሮጀክቱ በአሁኑ ጊዜ 2 ሺህ ሔክታር መሬት የማልማት አቅም ያለው ሲሆን፣ በአካባቢው የሚገኝ ተጓዳኝ የመስኖ ፕሮጀክት ሲጠናቀቅ ደግሞ 15 ሺህ ሔክታር መሬት ማልማት እንደሚችል ተገልጿል።
አዲስ አበባ ፣ (ኤፍ ቢ ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድና የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ በባቱ ከተማ የሚገኘውን ፍሎራ ቬጅ የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኝ ማፍያን ጎበኙ።
ፍሎራ ቬጅ በዓመት 20 ሚሊየን የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞችን በማፍላት ለአርሶ አደሩ የሚያቀርብ ሀገር በቀል ችግኝ ማፍያ ጣቢያ ነው።
ጣቢያው በግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚ ትልቅ ትኩረት የተሰጠውን የመስኖ ልማት በማገዝ ረገድ ትልቅ ሚና እንደሚጫወት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ተናግረዋል።
በ4 ሚሊየን ብር የተቋቋመው ይህ ተቋም ከ20 እስከ 30 ባሉት ቀናት ውስጥ የሚደርሱ የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞችን በማፍላት ለአርሶ አደሩ የሚያቀርብ ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይም ለአርሶ አደሩ የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኝን እያፈላ እያቀረበ ያለውን ፍሎራ ቬጅን ያበረታቱ ሲሆን አቅሙን በማሳደግ አቅርቦቱን እንዲጨምር ጠይቀዋል።
በጸጋዬ ንጉስ