World News

Goolgule.com: ሕዝብ “በጠብመንጃ መገዛት በቃን” አለ!! ትውልድ እንዳመጸ ነው!

Posted by: Berhane Habtemariam

Date: Thursday, 24 August 2017

ሕዝብ “በጠብመንጃ መገዛት በቃን” አለ!! ትውልድ እንዳመጸ ነው!

 
  • ለፖለቲከኞች እስር እውቅና የሰጡ “ፓርቲዎች” እየተደራደሩ – ሕዝብ እያመጸ ወዴት?

“እንወክለዋለን” በሚሉት ሕዝብ ዘንድ እውቅና ያላቸው ተቀናቃኝ ፓርቲዎች እጅግ አነስተኛ እንደሆኑ ይነገራል። አብዛኞቹ በምርጫ ቦርድ እውቅና ያገኙት የፖለቲካ ፓርቲዎች “ጥቂት” ከተሰኙት ውጪ ስለመኖራቸው እንኳን እንደማይታወቁ በተደጋጋሚ አስተያየት ይሰጣል። እነዚህን ፓርቲዎች ሰብሰቦ ድርድር መቀመጥ የአገሪቱን ችግር ማስተንፈስ እንደማይቻል የሚከራከሩ ወገኖች ድርድሩን አያከብሩትም። በሌላ በኩል ደግሞ ህወሓት/ኢህአዴግ እዚህ ደረጃ መምጣቱ በራሱ አንድ ርምጃ ነው የሚሉና ድጋፋቸውን የሚሰጡ ጥቂት አይደሉም። በውጤቱ ሲታይ ግን አመጹም፣ ቅሬታውም፣ ችግሩም መልኩን ሲቀያይር እንጂ ሲለዝብ ማስተዋል አልተቻለም።

ለዚህም ይመስላል የኦፌኮ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ሙላቱ ገመቹ “ከሚመለከታቸው ወገኖች ጋር ቁጭ ብሎ ከመወያየት ሌላ አማራጭ የለም” ሲሉ ለቪኦኤ የተናገሩት። የፖለቲካ መፍትሄ ለመፈለግ ንግግር እየተደረገ ባለበትና “ተደራዳሪ የሚባሉት” ብዙ ርቀት መሄዳቸውን በሚናገሩበት ወቅት “ሌላ አማራጭ የለም” ሲሉ አቶ ሙላቱ መፍትሄ ስለሚያስገኝ እውነተኛ ድርድር መናገራቸው ለንግግሩ እውቅና የመንፈግና መፍትሄ እንደማያመጣ አመላካች ስለመሆኑ ሂደቱን የሚከታተሉ የሚሰጡት አስተያየት ነው።

ህወሓት/ኢህአዴግ እና ተደራዳሪዎቹ ፓርቲዎች እያካሄዱት ካለው ድርድር በአገሪቱ ዴሞክራሲ እንዲጎለብት የሚያስችል ውጤት እንደሚገኝ፣ ፍትሃዊ ምርጫ የሚደረግበት አግባብ እንደሚፈጠር፣ እንዲሁም የመቻቻል ሃሳብና የፖለቲካው ምህዳር እንደሚሰፋ ተስፋ በሚሰጡበት ወቅት በአማራና በኦሮሚያ ተደጋጋሚ አድማ መካሄዱ የድርድሩን ውጤት ከወዲሁ አመላካች አድርጎታል። በዚህ ጉዳይ ላይ ቀደም ሲል ጀምሮ የሚሰጠው አስተያየት ሲጠቃለል “የሚሰሙና ተቀባይነት ያላቸው ፓርቲዎች ችግሩ ከመከሰቱ በፊት ያቀረቡት የድርድር ጥያቄ ተቀባይነት አግኝቶ ቢሆን ኖሮ፣ ህዝቡን አርፈህ ተቀመጥ፣ የድርድሩን ውጤት ጠብቅ በማለት ሊገስጹት በቻሉ ነበር። ከዚህም በላይ አመጹን ለመቆጣጠር በተወሰደው የሃይል ርምጃ የጠፋውን ሰብዓዊና ቁሳዊ ውድመት ማስቆም በተቻለ …”

የእንደራደር ጥያቄ ቢኖርም በተለያየ ወቅት አግባብ ያለው ምላሽ ባለማግኘቱ፣ የአገሪቱ ፖለቲካ ምህዳር መጥበቡና የዴሞክራሲ መብቶች መገደባቸው ጋር ተዳምሮ ዛሬ ላይ ደርሷል። ይህ ክልላዊ ስሜት የተላበሰው አመጽ ህወሓት/ኢህአዴግን እንደ አገዳ ውስጥ ውስጡን ሲበላው ቆይቶ ዛሬ ሲፈነዳ “በጥልቅ ተሃድሶ በአስር ሺህ የሚቆጠሩትን አባሎቼን አባረርኩ” በማለት አደባባይ አባላቱ እንደተንሸራተቱበት በራሱ አንደበት ለማመን ተገዷል።

ኢህአዴግ “ራሴን አጽድቼ፣ የመልካም አስተዳድር ችግሮችን ፈትቼ፣ የፖለቲካ ድርድር አካሄጄ፣ ለስራ አጦች በቢሊዮን ብር መድቤ፣ የኢንዱስትሪ አብዮት አካሂጄ፣ ታርሜና ታድሼ…” በማለት ከአመጹ ማግስት ጀምሮ ቃል እየገባ ቢመጣም ቦግ ድርግም የሚለው አመጽ ግን እየሰፋና መልኩን እየለወጠ፣ በስልትም እየጠለቀ መሄዱን ገለልተኛ ወገኖች እየመሰከሩ ነው። “ታድሼያለሁ፣ ቀድሞ የከዱኝን አባርሬ አዲስ ቁርጠኛ አባላትን መልምዬ ለሃላፊነት አብቅቻለሁ” ቢልም የክልላዊ አስተሳሰብ በዜናና በፕሮፓጋንዳ እንዲሁ በቀላሉ የሚተን ባለመሆኑ ሌላ ኢህአዴግ አማራጭ ፖለቲካዊ ርምጃ መወሰዱ እንደሚሻለው አገር ወዳዶች እየመከሩ ነው።

ከማስተር ፕላን ጋር በተያያዘ የተጀመረው የኦሮሚያ ሕዝባዊ አመጽ አድማሱን ወደ አማራ ክልል በማስፋት በማንነት ጥያቄ ሲታጀብ የፈጠረው ድንጋጤ አሁን ድረስ እንዳለ ነው። ኢህአዴግ አመጹ የተቀጣጠለው በራሱ ችግር እንደሆነ አምኖ የማስተር ፕላኑን ሃሳብ መጣሉን በማወጅ የኦሮሚያን ተቃውሞ ሊያስተነፍስ ቢሞክርም አልሆነም። አሁን እንደሚነገረውና የዓይን ምስክሮች እንደሚሉት ሶስተኛ የተባለ ሕዝባዊ አመጽ ተጀምሯል። በአማራ ክልልም በተመሳሳይ ከቤት ውስጥ ያለመውጣት አድማ ለማስጀመር ዝግጅት እንዳለ እየተሰማ ነው።

“ቄሮ የኦሮሞ ወጣቶች” የሚባሉትን የህቡዕ አደራጆችን በመጠቀስ ከዛሬ ጀምሮ ለአምስት ቀን የታወጀው ስርዓቱን የመቃወምና ቤት ውስጥ የመቀመጥ አድማ ተግባራዊ የሆነባቸው ከተሞችን በመዘርዘርና የዓይን እማኞችን በማነጋገር “ገለልተኛ” የሚባሉ ሚዲያ ይፋ አድርገዋል። የኦሮሚያ ሚዲያ ኔት ዎርክ እና ኢሳት ለዜናው ቅድሚያ ቢይዙም ቪኦኤ ዛሬ ማምሻውን አዲስ አበባ በሚገኘው ዘጋቢው አማካይነት ሃተታ አቅርቧል።

በዚሁ ዜና ላይ እንደተመለከተው ከሻሸመኔ፣ ከአምቦ፣ ከነቀምት እማኞች ስማቸው እንዳይጠቀሰ ጠይቀው ያዩትን ተናገረዋል። ሶስቱም የአይን ምስክሮች እንዳሉት የአድማው ምክንያት የታሰሩ የፖለቲካ መሪዎቻችን ይፈቱ፣ ያላ አግባብ የተጣለው የገቢ ግብር ይነሳ፣ በኦሮሚያና ሶማሌ ክልል የሚፈሰውን ደምና የድንበር ግጭት መንግስት ያስቁም የሚሉ ናቸው። የሻሸመኔው አስተያየት ሰጪ ግን “ህዝቡ በጠመንጃ አፈሙዝ አንገዛም ነው የሚለው” ሲሉ ተደምጠዋል።

በሻሸመኔ ሁለት ሆኖ መራመድ እንደማይቻል፣ እቤት ውስጥ አድሞ መቀመጥ ክልክል መሆኑንን፣ ታጣቂዎች ቤት ድረስ እየገቡ እንደሚደባደቡና በግድ ውጡ እንደሚሉና በከተማው በግድ ሱቅ ክፈቱ በሚል ማስፈራራት ይደረግ እንደነበር አስረድተዋል።

የነቀምቴው አስተያየት ሰጪ የመንግሥት ሰራተኛ መሆናቸውን ተናገረው “አንድ ሁለት ሱቆች ተከፍተው ነበር” ካሉ በኋላ፣ ከአድማው መጀመር አንድ ቀን በፊት ካቢኔው ተሰብስቦ የመንግሥት ሰራተኞች ከስራ ቢቀሩ እንደሚታሰሩና ከስራ እንደሚባረሩ ማስፈራሪያ በአለቆች በኩል መላካቸውን ተናግሯል።

ከአዲስ አበባ ዙሪያ የኦሮሚያ ከተሞች ጀምሮ በተለያዩ የኢትዮጵያ ከተሞች የተጀመረው የቤት ውስጥ መቀመጥ አድማ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል፣ ውጤታማ እንደሚሆንና ተከታታይ የተጠኑ ስልቶች እንደሚተገበሩ እንቅስቃሴውን ከዳያስፖራ ሆነው ይመራሉ የሚባሉ ወገኖች ሲናገሩ ተደምጧል።

ሌንጮ ለታ የሚመሩት የኦዴግ ከፍተኛ አመራር የሆኑት በያን አሶባ በበኩላቸው ትግሉ ሁሉን አቀፍ በመሆኑ መላውን አገሪቱን በሚያስተባበር መልኩ ሊቀጥል እንደሚገባ አመልከተዋል። በኢሳት አማካይነት ከአንድ ቀን በፊት ድምጻቸውን ያሰሙት ዶ/ር በያን ትግሉ የመላው ኢትዮጵያውያን እንደሆነ መጠቆማቸውን ተከትሎ አድማው በአማራ ክልልም ለማስጀመር ዝግጅት መጀመሩን ለማወቅ ተችሏል።

የዛሬ ዓመት የኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጠኛ JEFFREY GETTLEMAN በኢትዮጵያ ያለው ወቅታዊ ሁኔታ የተነተነበትን ጽሁፍ ጎልጉል ባቀረበበት ወቅት ይህን የጋዜጠኛውን ቃል ጠቅሶ ዘግቦ ነበር፤ “ሕዝቡን ካፈንከው እና ከመቃወም ሌላ አማራጭ ካሳጣኸው ይፈነዳል፤ ወጣቱ በሙሉ ዓመጽ ላይ ነው፤ ትውልድ አምጿል”፡፡ (ከዜና ዘገባው ጋር Violent Protests in Ethiopia በሚል ርዕስ የጸጥታ ኃይሎች ሰላማዊ ሰልፍ በወጣ ህዝብ ላይ የሚፈጽሙትን  አሰቃቂ ግፍ እና ጨካኝ ድብደባ እዚህ ላይ መመልከቱ የግድ ይላል)፡፡

ይህንን መሰሉን ግፍ እና በጠብመንጃ የታገዘ የግፍ አገዛዝ ሕዝብ አልቀበልም ማለቱ የሚጠበቅ እንጂ የሚያስገርም ጉዳይ አለመሆኑን የሚናገሩ ወገኖች፤ በአማራና በኦሮሚያ መካከል የትግል ትብብር ማድረግ የህወሓት/ኢህአዴግን ጉልበት እንደሚያርደው አሁንም ይመክራሉ፡፡ ባለፈው በተነሳው ሕዝባዊ ተቃውሞ ይህ መሰሉ ትብብር ያስደነገጠው ህወሓት በተጨነቀበትና በሚዲያ ወጥቶ ራሱን ባጋለጠበት ወቅት በተለይ ከዳያስፖራ የሚነዛ የነበረው በዘር የመከፋፈል ጠባብ አስተሳሰብ ህወሓት/ኢህአዴግን እንደገና እንዲሰነብት አስችሎታል ይላሉ፡፡ ሕዝብ በጠብመንጃ አልገዛም ካለ ቆይቷል፤ ወጣቱ ትውልድም አምጿል፤ ፖለቲካውን እንመራዋለን የሚሉት ግን ይህ የገባቸው አይመስልም ወይም በአፋቸው ሕዝባዊ በልባቸው ግላዊ ሆነዋል፡፡


EmbassyMedia - ራብዓይ ግንባር!

Dehai Events