World News

ዶይቸ ቬለ / በሐማሬሳ ግጭት 4 ሰዎች ሞተው 11 ቆሰሉ

Posted by: Semere Asmelash

Date: Tuesday, 13 February 2018

ኢትዮጵያ  ቀን 12.02.2018

በሐማሬሳ ግጭት 4 ሰዎች ሞተው 11 ቆሰሉ

በሐማሬሳ የተፈናቃዮች መጠለያ ስፍራ ትላንት በተቀሰቀሰ ግጭት ሰዎች መሞታቸው እና መቁሰላቸውን የአካባቢው ባለስልጣናት ለዶይቼ ቬለ ገልጸዋል፡፡ በመጠለያ ጣቢያው ዛሬም ተቃውሞ ቀጥሎ እንደነበር እና በአቅራቢያው በሚገኘው የሀሮማያ ዩኒቨርስቲ ለተቃውሞ የወጡ ተማሪዎች በጸጥታ ኃይሎች እንዲበተኑ ተደርጓልም ተብሏል፡፡
በሐማሬሳ የተፈናቃዮች መጠለያ ትላንት በተቀሰቀሰው ግጭት አራት ሰዎች ሞተው 11 ሰዎች መቁሰላቸውን የምሥራቅ ሐረርጌ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ጀማል አህመዴ ለዶይቼ ቬለ ገለጹ፡፡ ወደ 3‚500 ገደማ የሚሆኑ ከሶማሌ ክልል የተፈናቀሉ የኦሮሞ ተወላጆች በተጠለሉበት በዚሁ ጣቢያ ዛሬም ተቃውሞ የነበረ ቢሆንም ጉዳት አለመድረሱንም ተናግረዋል፡፡ 
የትናንትናው ግጭት የተነሳው እህል ጭነው እየተጓዙ የነበሩ መኪኖች “በማይታወቁ ሰዎች ተይዘው ወደ ተፈናቃዮች መጠለያ እንዲገቡ በመደረጋቸው” እና የጸጥታ ኃይሎች እነርሱን ለማስለቀቅ ባደረጉት ሙከራ እንደነበር ተናግረዋል፡፡ ከዚያ በኋላ የተፈጠረውን ደግሞ እንዲህ አስረድተዋል፡፡  
“የፌደራል የጸጥታ አካላት እና የክልል ጸጥታ አካላት (የሐረሪ እና የምስራቅ ሐረርጌ ዞን) አሉ፡፡ መጨረሻ ላይ እዚያ መከላከያ ገብቶ ነበር፡፡ እንግዲህ በዚህ መካከል በተፈጠረ ችግር ነው የሰው ህይወት ሊጠፋ የቻለው፡፡ ያንን መኪና ለማስለቀቅ በሚመጡ እና እዚያ መሃል ባለው ያው የሰው ህይወት ሊጠፋ ችሏል፡፡ አራት [ሰዎች]  ህይወታቸው ሲያልፍ ወደ 11 የሚሆኑ የቆሰሉት ናቸው” ብለዋል፡፡  
ከሟቾቹ ውስጥ አንድ የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ አባል እና አንዲት ሴት እንደሚገኙበት አቶ ጀማል አስረድተዋል፡፡ በትናትናው ግጭት የቆሰሉት በሐረር ፋና ሆስፒታል ሕክምናቸውን እየተከታተሉ እንደሚገኙ የተናገሩት አቶ ጀማል ቁስለኞቹ በደህና ሁኔታ ላይ እንደሚገኙም ገልጸዋል፡፡ የሐረሪ ክልል ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ዛሬ በይፋዊ የፌስ ቡክ ገፁ ላይ ባወጣው መግለጫ በሐማሬሳው ሁከት ሰባት እህል ጭነው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ከባድ መኪኖች እና ማሽኖች መቃጠላቸውን አስታውቋል፡፡ ድርጊቱ የፈጸሙት “የተደራጁ የፀረ ሰላም ኃይሎች” ነው ሲል ከስሷል።   
በሐማሬሳ መጠለያ ጣቢያ ዛሬም ተቃውሞ እንደነበር ከአካባቢው የሚወጡ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በጣቢያው ተቃውሞ እንደነበር ያረጋገጡት አቶ ጀማል በግቢው ያሉ የመከላከያ ኃይሎች እንዲወጡ በመጠየቅ የተደረገ እንደሆነም አስረድተዋል፡፡ የዛሬውን ውሎ አስመልክቶም “ያለው ሁኔታ ጠዋት በግቢው የተወሰነ ግርግር ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ የኦሮሚያ ክልል ፖሊሶች ገብተው ግቢውን እየጠበቁ ናቸው ያሉት፡፡ አሁን ከሀዘን ውጭ የተረጋጋ ሁኔታ እየተፈጠረ ነው ማለት ይቻላል” ብለዋል፡፡
12.06.2013 DW Online Karten Basis Äthiopien Englisch
ከሐረር ከተማ አምስት ኪሎ ሜትር ርቀት ገደማ ላይ የሚገኘው የሐማሬሳ መጠለያ ጣቢያ በሐረሪ ክልል ስር የሚገኝ ቢሆንም የጣቢያውን ጸጥታ ይቆጣጠር የነበረው እና ለተፈናቃዮች እርዳታ የሚያቀርበው የኦሮሚያ ክልል ነበር፡፡ የትላንትናውን ግጭት ተከትሎ በስፍራው ላይ የተገኙት የመከላከያ ሠራዊት አባላት «እንዴት ወደ ቦታው እንደመጡ መረጃው የለኝም» ሲሉ የምሥራቅ ሐረርጌ ዞን አስተዳዳሪ ለዶይቼ ቬለ ተናግረዋል፡፡ የመከላከያ ሠራዊት አባላቱ «ግጭቱን በሌላ መልኩ ከመቆጣጠር ይልቅ የኃይል እርምጃ ወስደዋል» ስለመባሉ ጠይቀናቸው ተከታዩን ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
“የችግሩ ሁኔታን ለማጣራት ብዙ ሰዓት ወስደን ስናጣራ ነበር፡፡ ሙሉ ዝርዝር መስጠት ስለማልችል ነው እንጂ ያየናቸው፣ የገመገምናቸው፣ በየቦታው የተፈጠሩ ችግሮች አይተናል፡፡ ከሶማሌ ክልል የተፈናቀሉ ኦሮሞዎች ያሉበት መጠለያ ነውና ለዚህ ነው የኦሮሚያ ፖሊስ እና ሌሎች የመስተዳድር አካላት እዚያ ላይ የሚሳተፉት እንጂ መስተዳድሩ የሌላ ክልል መስተዳድር እንደሆነ ብንገነዘብ ጥሩ ነው፡፡ አጠቃላይ ስለ እዚህ የምንግራችሁ ሌላ ቦታም ችግሮች ይከሰታሉ፤ እርሱ በራሱ መንገድ እየተጣራ ነው፡፡ በኦሮሚያ [ክልላዊ] መንግስትም፣ በሌሎች በኦህዴድም፣ በኢህአዴግም አጣርቶ ያው አቅጣጫ እየተቀመጠበት ነው ያለው፡፡ ከዚያ ውጭ ትላንትና በተፈጠረው ሁኔታ ጉዳዩ ተጣርቶ፣ በትክክልም የሰው ህይወት ያጠፋ አካል ተጠያቂ መሆን እንዳለበት የሁላችንም አቋም መሆን እንዳለበት መረዳት ጥሩ ነው ለማለት ነው” ይላሉ የዞኑ አስተዳዳሪ።
በሐማሬሳ ግጭት ሰዎች መሞታቸውን በመቃወም እና የታሰሩ ሰዎች እንዲፈቱ ለመጠየቅ ከመጠለያው አቅራቢያ በሚገኘው ሀሮሚያ ዩኒቨርስቲ ያሉ ተማሪዎች ዛሬ ተቃውሞ አሰምተው ነበር፡፡ ተቃውሞ እንደነበር ያረጋገጡት አቶ ጀማል ተማሪዎችን ለመበተን ጥይት ተተኩሷል መባሉን ግን ያስተባብላሉ፡፡ የተተኮሰው ጥይት ሳይሆን የተሰበሰቡ ሰዎችን ለመበተን አገልግሎት ላይ የሚውለው «አስለቃሽ ጭስ ነው» ባይ ናቸው፡፡ ከምሥራቅ ሐረርጌ ዞን የሄዱ አመራሮች በስፍራው ተገኝተው ሁኔታውን ለማረጋጋት መሞከራቸውንም አስረድተዋል፡፡  
ተስፋለም ወልደየስ
ሸዋዬ ለገሠ
-----

በኦሮምያ የተጠራዉ አድማ

በኦሮሚያ ክልል ከዛሬ ጀምሮ ለሦስት ቀናት የሚዘልቀዉ የንግድ ወይም የግብይት እንቅስቃሴ ላይ የተጠራው አድማ ተግባራዊ መሆን መጀመሩን ከተለያዩ ቦታዎች በመደወል ያሰባሰብናቸው መረጃዎች ያመለክታሉ።
አድማዉ የተዘጋጀዉ «ቄሮ እና ቃሬ» በመባል በሚታወቁት የክልሉ ወጣቶች መሆኑ ሲነገር፤ የፖለቲካ እስረኞች ያለ ቅድመ ሁኔታ እንዲፈቱ፣ በክልሉ ያለዉ የመከላከያ ሠራዊት ለቅቆ እንዲወጣ፣ የዜጎች ግድያ እንዲቆም የሚሉ እና ሌሎችም ጥያቄዎች መቅረባቸውን ለመረዳት ተችለዋል።
የማኅበራዊ መገናኛ ብዙሃን ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት ከሆነ አድማዉ በክልሉ ያሉትን 19ኙንም ዞኖች አካልሏል። በዚህም ከአዲስ አበባ በአራቱ መዉጫዎች ማለትም በአዳማ፣ በሱሉልታ፤ ሰበታ እና አምቦ መስመሮች የተሽከርካሪዎች እንቅስቃሴ መቋረጡን ከአካባቢው ነዋሪዎች ለመረዳት ተችለዋል። የአዲስ አበባ ነዋሪ የሆኑ አንድ አድማጭ በዋትስ አፕ በላኩልን ጥቆማ መሠረት ሚስታቸዉ አምቦ ዩኒቨርሲቲ እንደሚማሩ ጠቅሰው ዛሬ ጥዋት ግን ወደዚያ ለመሄድ መጓጓዣ እንዳላገኙ ገልፀዉልናል። በተመሳሳይም በሌሎች ቦታች የሚኖሩ ግን ስማቸዉ እንዲጠቀስ ያልፈለጉ ግለሰቦች ያዩትን እና የሰሙትን እንዲህ አጋርተውናል።
ወጣቶቹ ያነሱት ጥያቄ የክልሉ መንግሥት አምኖ ተቀብሎ ለመፍታት እየሞከረ መሆኑን የሚናገሩት በኦሮሚያ ክልል በፍትህ ቢሮ የኮሙኒኬሼን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ታዬ ዳንዳኣ አድማዉ ትክክል ነዉ ብለን አናስብም ይላሉ። አቶ ታዬ: «በማይፈለግ መንገድ ተኬዶ የግብይት አድማ መጥራት ትክክል ነዉ ብለን አናስብም። ይሁን እንጅ አድማዉ ከተጠራ፣ ሰዉ ይሄን ለማድረግ መብቱ ስለሆነ፣ ጉዳዩ ወደ ያልተፈለገ አቅጣጫ እንዳያመራ የፀጥታ አካሎች በሰላም ጠብቆ፣ አረጋግቶ፤ በሰላም እንዲጠናቀቅ እንፈልጋለን።»
የኦሮምያ እና የኢትዮጵያ ሶማሊ አዋሳኝ ድንበሮች ላይ በተፈጠረዉ ግጭት ምክንያት ከቄያቸዉ ተፈናቅለዉ በሐረሪ ክልል ስር ብትገኝም በምሥራቅ ሐርሬጌ ዞን በኦሮሚያ ክልል የሚተዳደረው የሐማሬሳ ካምፕ ውስጥ ተጠልለው የሚገኙት ላይ የመከላክያ ሠራዊት ትናንት ወስዷል በተባለው የኃይል ርምጃ ሰዎች መሞታቸው እና መቁሰላቸው ተገልጿል። ዛሬም ወጣቶች መንግሥት ቃሉን እያከበረ አይደልም የሚል እና ሌሎች ተቃዉሞች ሲያሰሙ እንደነበረ የዓይን እማኞች ይናገራሉ። የኦሮሚያ የፍትህ ብሮ የኮሙኒኬሼን ጉዳዮች ኃላፊ የሐማሬሳዉ ክስተት ኅብረተሰቡን አያናድድም ማለት እንደማይቻል አስረዳሉ።
አቶ ታዬ: « ትላንት የሆነ ጉዳይ እኛ እንደ መንግሥት ወንጀል መሆኑን እናምናለን። በመጀመርያ ደረጃ በሕግ እንደምናዉቀዉ መከላከያ ድንበር እንጅ ከተማ አይጠብቅም። በአከባቢዉ የተፈጠረ ትልቅ ችግር የለም። ሕህል የጫነ መኪና እዚህ ካምፕ ይግባ ብሎ ያዙት የሚባል ነገር አለ። በባዶ እጃቸዉ የወጡ ሰዎችን ግንባር ላይ መትቶ እስከመግደል ደረጃ ደርሰዋል። ጭካኔ በተሞላ የተደረገ ድርጊት ነዉ፣ ይህ ትክክል አይደልም። በፍትም እንድህ አይነት ድርግት ተፈፅመዋል። ይጠየቃሉ ተብሎ ሳይጠየቁ እስካሁን አሉ። የክልሉ መንግሥት በዚህ ጉዳይ ላይ አጠናክሮ በመከታተል ይህን ድርጊት የፈፀሙ ተለይተው  እንዲጠየቁ ያደርጋል። በእርግጥ እንዲህ አይነት ወንጀል ሲፈፀም ማህበረሰቡን አያናድድም ማለት አይቻልም፤ ይህ አሳፋሪና ሆድን የሚያቃጥል ስለሆነ።»
የግብይት አድማዉን ተከትሎ እየተካሄደ ባለዉ ተቃዉሞም የፀጥታ አካሎች በወሰዱት ርምጃ የሰዉ ሕይወት መጥፋቱንም የማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች እየገለጹ ነው።
መርጋ ዮናስ
ሸዋዬ ለገሰ 













EmbassyMedia - ራብዓይ ግንባር!

Dehai Events