የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ የአልጄርስ ስምምነትን ለመቀበል መወሰኑን ተከትሎ ጉዳዩ አነጋጋሪ ሆኗል። በተለይ በአንዳንድ የትግራይ አከባቢዎች የአልጄርስ ስምምነት በመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ ተደርጓል። ለዚህ ደግሞ በምክንያትነት ከሚጠቀሱት ውስጥ፤ በተለይ ባድመ ላይ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ የኢትዮጵያ ወታደሮች መስዕዋት ሆነዋል፣ በአከባቢው የሚኖሩ የማህብረሰቦችን ለሁለት ይከፍላል፣ እንዲሁም የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ በሀገሪቱ መሬትና ሉዓላዊነት ላይ በተናጠል የመወሰን ስልጣን የለውም እና ስምምነቱን ለመቀበል ሕዝበ ውሳኔ መደረግ አለበት የሚሉት በዋናነት ይጠቀሳሉ። ከዚህ አንፃር “የኢህአዴግ መንግስት የአልጄርስ ስምምነትን ተቀብሎ ተግባራዊ ሊያደርግ አይገባም” የሚል መከራከሪያ ያቀርባሉ።
ሆኖም ግን፣ “የጉድ ሀገር ጉድ እያደር ይወጣል” እንደሚባለው፣ ከአልጄርስ ስምምነት ጋር በተያያዘ ሌላ አዲስ ጉድ ወጥቷል። ይኸውም የኢፌዲሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የአልጄርስ ስምምነትን ተቀብሎ አፅድቆታል። ህዳር 29/1993 ዓ.ም በፌዴራል ነጋሪት ጋዜጣ 7ኛ ዓመት ቁጥር 7 ታትሞ በወጣው አዋጅ ቁጥር 225/1993 መሰረት በኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክና በኤርትራ መንግስት መካከል የተደረገው የሰላም ስምምነት በኢፌዲሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጸድቋል።
በኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክና በኤርትራ መንግስት መካከል በአልጄሪያ ዋና ከተማ አልጄርስ የተደረገውን የሰላም ስምምነት ለማፅደቅ የወጣው አዋጅ ቁጥር 225/1993 የኢፌዲሪ ሕገ መንግስት አንቀፅ 55 ንዕስ አንቀፅ 1 እና 12ን መሰረት ባደረገ መልኩ እንደሆነ በአዋጁ ተጠቅሷል። አንቀፅ 55 (1) የኢፌዲሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሕገ መንግስቱ መሰረት ለፌደራል መንግስት በተሰጠው የስልጣን ክልል ውስጥ ሕጎችን ያወጣል በማለት ይደነግጋል። አንቀፅ 55(12) ደግሞ የኢፌዲሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት “የህግ አስፈፃሚው አካል የሚዋዋላቸውን ዓለም-አቀፍ ስምምነቶች ያፀድቃል” ይላል።