Dehai News

Zehabesha.com: ሙስና ብርቅ ነው ወይ? |

Posted by: Berhane Habtemariam

Date: Thursday, 27 July 2017

ሙስና ብርቅ ነው ወይ? |

ቬሮኒካ መላኩ


“መስረቅ ስራ ነው ።ከተያዝክ ግን ወንጀል ነው ” ይሄን በአንድ ወቅት የተናገረው የቀድሞው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ነው።

ከዛሬ ሦስት ሺህ አምስት መቶ ዓመት በፊት የሙሴ ሕግ ጉቦ መቀበልን አውግዟል። ከዚያ በኋላ በነበሩት መቶ ዘመናት በርካታ ፀረ ሙስና ሕጎች ተረቅቀዋል። ያም ሆኖ ግን የተደነገጉት ሕጎች ሙስናን በመግታት ረገድ ስኬታማ ሊሆኑ አልቻሉም። በየቀኑ በሚልዮን የሚቆጠሩ ጉቦ የመስጠትና የመቀበል ወንጀሎች የሚፈጸሙ ሲሆን በዚህ ጦስ በቢልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ይሠቃያሉ።

አርኖ ሞንትበር የተባለው ፈረንሳዊ የህግ ባለሙያ “ሙስና የሰዎችን መንፈስ እንደሚጫጫን መጠነ ሰፊ የአየር ብክለት ሊመሰል ይችላል” በማለት ገልፇታል ።

The Economist የተባለው የብሪታኒያ መጽሔት እንደዘገበው ደሞ ” በየዓመቱ ለዓለም አቀፍ ንግድ ከሚውለው 25 ቢልዮን የአሜሪካ ዶላር ውስጥ 10 በመቶ የሚሆነው አዳዲስ ደንበኞችን ለማፍራት በጉቦ መልክ የሚሰጥ ነው ።”

ወደ ኢትዮጵያ የሙስና ሁኔታ ስንመጣ ለመጀመሪያ ጊዜ ሙስና ተቋማዊ መልክ ኖሮት በመላ አገሪቱ እንድናኝ ያደረገው ህውሃት ወያኔ ነው። በአለም ታሪክም ለመጀመሪያ ጊዜም የአገር መሪ ሆኖ የድለላ ኮሚሽን ብር የተቀበለው መለስ ዜናዊ ነው። መለስ ዜናዊ ያራ ከተባለ የኖሮዌ የማዳበሪያ ፋብሪካ ካለጨረታ ማዳበሪያ እንድያቀርብ ካስደረገ በኋላ የደለለበትን የ20 ሚሊዮን ዶላር ቼክ ወስዷል። በኋላ የአለም መሪዎች ሲስቁበት ከያራ ያገኘውን የድለላ ኮሚሽን ለችግረኛ ሴቶች ሰጥቻለሁኝ ማለቱ ይታወሳል።

ደርግ እና ሙስና አይተዋወቁም ነበር ብሎ ደፍሮ አፍን ሞልቶ መናገር ይቻላል። የደርጉ ሊቀመንበርና የአገሪቱ መራሄ መንግስት የነበረው መንግስቱ ሃይለማሪያም ለአመታት ይጠቀምበት የነበረው የቤት እቃ ከሀረር ይዞት የመጣውን ከቀርከሃ የተሰራ ሶፋ ሲሆን የሚታኛበትም ተራ ሽቦ አልጋ እንደነበር በደርግ ዘመን ባለስልጣን የነበረ ዘነበ ፈለቀ የተባለ ሰው በመፅሃፉ ፅፎ አንብቤለሁኝ።
ዛሬ በደርግ ዘመን የአገሪቱ ሁለተኛ ሰው የነበረው ጠቅላይ ሚኒስትር ፍቅረስላሴ የሚኖረው በኪራይ ቤት ነው። ዛሬ አንድ ስሙ ሀጎስ የሚል መጠሪያ ያለው የወያኔ አስር አለቃ ወይም ስሙ በርሄ የሆነ የባለስልጣን ሹፌር አዲስ አበባ ከተማ ቪላቤት ሲገነባ መመልከት የአደባባይ ምስጢር ነው።

ኢትዮጵያ ውስጥ ሙስና እጅግ ከመስፋፋቱና በዓይነቱ በጣም እየረቀቀ ከመምጣቱ የተነሳ ኅብረተሰቡ የተገነባበትን መዋቅር እያሽመደምደው ነው። ዛሬ የትኛውም የመንግስት ቢሮ በእጅ ካልተሄደ ምንም ነገር ማስፈጸም አይቻልም ለማለት ያስደፍራል። ሙስና በከፍተኛ ፍጥነት እየተስፋፋ ከመሄዱ የተነሳ በጣም የተለመደ ነገር እስከመሆን ከመድረስ አልፎ ይበልጥ ተቀባይነት እያገኘ ነው ። በጣም አነስተኛ ክፍያ የሚያገኙ ሰዎች ሌላ አማራጭ እንደሌላቸው ማሰብ ይጀምራሉ።

ሙስናን እንዲባባስ እያደረጉ ያሉ ሁለት ብርቱ ኃይሎች አሉ። እነዚህም ራስ ወዳድነትና ስግብግብነት ናቸው። ምግባረ ብልሹ የሆኑት የወያኔ ሰዎች ራስ ወዳድ ከመሆናቸው የተነሳ በሙስና መካፈላቸው በሌሎች ላይ የሚያመጣውን መከራ ችላ ብለው አገሩን በሌብነት አግማሙት ። እነዚህ በሙስናና በሌብነት የተዘፈቁ ዘረኞች ይበልጥ ቁሳዊ ነገሮች ባካበቱ መጠን ይበልጥ ስግብግብ እየሆኑ ይሄዳሉ።


ሰሎሞን እንዲህ ብሏል:- “ብርን የሚወድድ ሰው ብርን አይጠግብም፤ ባለጠግነትንም የሚወድድ ትርፉን አይጠግብም።” (መክብብ 5:10) እርግጥ ስግብግብነት ገንዘብ የሚያስገኝ ቢሆንም በተቃራኒው ሞራለ ቢስ እና ዘራፊ እና ሃሞተ ቢስ ትውልድ የማፍራት ጉዳቱ ከፍተኛ ነው።

ህውሃት ሙስናን የታማኝነት ማረጋገጫ መያዣ Hostage አድርጎ እንደሚጠቀምበት ይታወቃል። ታማኝ ሎሌ ከሆንክ 70 ቢሊዮን ብትበላ ፣ፎቅ እንደ ችግኝ ብትተክል ዝንብህን እሽ የሚል ሰው የለም። ከሎሌነት ውርደት ልውጣ ብለህ ጉዞ ከጀመርክ ግን ቤትህ ውስጥ ይገባል ብለህ በህልምህም በእውንህም አስበህ የማታውቀውን ሚሊዮን ብር ሰባራ ሶፋህ ስር ያስቀምጡና እጅ ከፍንጅ ተያዘ ብለው ዜና ሰርተውብህ ዘብጥያ ይወረውሩሃል።


ጉልበት ፣ ሃይልና መሳሪያ ንፅህናና ቅድስና በሆነባት አገር ትልቁ ነገር አለመቀደም ነው። የሰሞኑም የሙስና ታፔላ የተሰጠው የአዳኝ ታዳኝ ድራማ ያሳየን ይሄንኑ ነው።

 

EmbassyMedia - ራብዓይ ግንባር!

Dehai Events